በኢትዮጵያ ከፍተኛ የንግድ መቀዛቀዝ እየታየ መሆኑ ተጠቆመ፡፡ በተለይ በውጭ ምንዛሪ እጥረት ምክንያትና የገዥው ኢህአዴግ የአየተከተለ ያለው የንግድ ስርዓት አድሎነት የተሞላበት ከመሆኑም በተጨማሪ ለስርዓቱ ከቀረቡት ጥቂት ነጋዴዎች እና ንብረትነቱ የህወሃት/ ኢህአዴግ እንደሆነ የሚነገርለት ኤፈርት ኩባንያ ውጭ ያሉ ነጋዴዎች ከአቅማቸው በላይ ግብር እየተጫነባቸው በመሆኑ የንግድ ስራቸውን ወደ ሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች እያዛወሩ መሆኑን ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ ኢትዮጵያውያን የኩባንያ ባለቤቶች አስታወቁ፡፡
እንደባለሃብቶቹ ገለፃ ከሆነ በአሁን ሰዓት ምንም ዓይነት የባንክ ብድር እንዳናገኝ አበዳሪ ባንኮች ለእኛ የሚያበድሩ ከሆነ ከሚያበድሩን ገንዘብ ላይ 27 በመቶ ለአባይ ግድብ እንዲያውሉ ጥብቅ መመሪያ በመተላለፉ ባንኮቹ ለማበደር ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ በዚህም ምክንያት በንግድ ስርዓቱ ላይ ከፍተኛ ችግር በመፈጠሩ በሀገሪቱ ላይ የዕቃ አቅርቦት ችግር እየተከሰተ መሆኑንም ለፍኖተ ነፃነት ገልፀዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ከውጭ ዕቃ ለማምጣት የውጭ ምንዛሪ የሚፈልግ ነጋዴ ከመደበኛው የአሜሪካን ዶላር ምንዛሪ ውጭ በአንድ ዶላር እስከ 25 ሳንቲም ተጨማሪ ክፍያ በህገወጥ መንገድ ለባንክ አስተዳደሮች እንዲሰጡ እየተገደዱ መሆኑን በማስታወስ እንደ ለስላሳ መጠጦች ኢንዱስትሪ ያሉትም ከውጭ ምንዛሪው እጥረት በተጨማሪ የስኳር አቅርቦት ችግር በመከሰቱ የምርት እጥረት መኖሩም ተጠቁሟል፡፡
ከላይ ተፈጠረ የተባለውን የንግድ ችግር በተመለከተ የንግድ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አማከለ ይማም በበኩላቸው “የተባለው ችግር አልተፈጠረም፣ ይህን በሚመለከት ጥያቄያችሁን በፅሑፍ ማቅረብ አለባችሁ” ከሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የተፈጠረውን የውጭ ምንዛሪ እጥረት በተመለከተ ደግሞ የብሔራዊ ባንክ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ደረጀ እንግዳው የውጭ ምንዛሪ እጥረትን በተመለከተ የባንኩ ገዥ እና ምክትላቸው ለኢቴቪ ከሰጡት ውጭ ሌላ ምላሽ እንደሌላቸው ለፍኖተ ነፃነት ገልፀዋል፡፡