በአዲስ አበባ በሚገኘው ቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ልዩ ስሙ ቦሌ ለሚ በሚባል አካባቢ ማክሰኞ መጋቢት 3 ቀን 2005ዓ.ም. ኮብልስቶን በሚሰሩ ሰዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት 8 ሰዎች መሞታቸውንና በርካታ ሰዎች መቁሰላቸው ተጠቁሟል፡፡ ከአካባቢው ምንጮቻችን የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው ከሆነ የግጭቱ መንስኤ የሞባይል መጥፋት እንደሆነ እና በዚህም ኮብልስቶን ትሰራ የነበረች የአንዲትን ሴት ጡት ሌላው ሰራተኛ በመቁረጡ ህይወቷ ማለፉን ተከትሎ በዛው ዕለት ፀቡን ለማረጋጋት የሞከረ ፖሊስም በኮብልስቶን ተመቶ ወዲያው ህይወቱ ማለፉን ጠቁመዋል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ ጉዳዩ ወደ ዘረኝነት ስሜት ተለውጦ ግጭቱ እስከ ሐሙስ መጋቢት 5 ቀን መዝለቁንና ህይወቷ ያለፈው ወጣት የአካባቢው ኦሮሚያ ተወላጅ በመሆኗ ጉዳዩ ወደ ማኀበረሰቡ በመድረሱ በርካታ የአካባቢው ሰዎች ከአያት ኮንዶሚኒየም እስከ ቦሌ ለሚ ድረስ ከበባ በማድረግ በሰራተኞች መካከል የኢህአዴግ አደራጅና ሰላይ ናቸው የተባሉ 6 ሰዎችን በመግደልና በርካታ ሰዎችን በማቁሰላቸው በአካባቢው ከ 3 ተሸከርካሪ ያላነሱ የፌደራል ፖሊሶች ግጭቱን ለማረጋጋት ቢገኙም እንዳልቻሉና በርካቶችንም ወስደው እንዳሰሩ የዓይን እማኞች ገልፀዋል፡፡ ይሁን እንጂ እስከ አሁን ከፖሊስ ወገን የተሰጠ ማረጋገጫ የለም፡፡ የዝግጅት ክፍሉ ጉዳዩ በቀጥታ ይመለከተዋል ወደተባለው ቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መረጃ ክፍል ስለጉዳዩ ለማረጋገጥ ተደጋጋሚ ጥረት ቢያደርግም አልተሳካም፡፡
ዘገባው ወደህዝብ እንዲደርስ እስከተደረገበት መጋቢት 7 ቀን 2005ዓ.ም. ድረስ ቀደም ሲል በርካታ ሰዎች የኮብልስቶን ስራ ይሰሩበት የነበረው አያት ጨፌ እና ቦሌ ለሚ የሚባል አካባቢ ማንም ሰው እንዳይገባ የተደረገ ሲሆን ከሰራተኞች ጋር እዛው በሚገኝ ቀበሌ ለጊዜው ማንነታቸው ያልታወቁ የመንግስት ባለስልጣናት እያወያዩ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡ ችግሩ እስኪፈታም በአካባቢው እስከ ሰኞ መጋቢት 10 ቀን 2005ዓ.ም. ድረስ ስራ እንደለሌም ምንጮቻችን ከስፍራው ጠቁመዋል፡፡ ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ በስፍራው የኮብልስቶን ስራ ላይ ተሰማርተው የነበሩና አሁን በውስጡ የቆየና እየተስፋፋ የመጣው የዘረኝነት ስሜት አስፈሪ ደረጃ ላይ የደረሰ በመሆኑ፤ ቀደም ሲልም ችግሩ እንዲቀረፍ ቢገለፅም ከማባባስ ውጭ መፍትሄ የሚሰጥ የመንግስት አካል ባለመኖሩ ዳግም ወደስራው እንደማይመለሱ በመግለፅ “ይህ ዜጎችን በዘረኝነት ከፋፍሎ የማጫረስ የአቶ መለስ ዕራይ ተጠናክሮ መቀጠሉን ያሳያል ሲሉ በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኞች ገልፀዋል፡፡