የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ስላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ትምህርታቸው ከመጋቢት 2 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ተቋርጧል፡፡በተማሪዎቹ በመማር ማስተማር ሂደት ወቅት በረካታ አስተዳደራዊ በደል እየደረሰባቸው እንደሆነና ለጥቄያቸው መልስ የሚሰጥ አካል ባለመገኘቱም ምግብ የመብላትና ትምህርት የማቆም አድማ ካደረጉ እነሆ ዛሬ 15 ቀን ሆኖኗቸዋል፡፡ የምግብ አድማ ካደረጉም በኋላ መጋቢት 16 ቀን 2005ዓ.ም. የ5ኛ ዓመት ደቀመዝሙር የሆኑት አባማቲያስ፣ የ2ኛ ዓመት በኃይሉ ሰፊ እና ገብረእግዚአብሔር የተባሉ የኮሌጁ ደቀመዛሙርት ታመው ወደ ሆስፒታል መሄዳቸው ተጠቁሟል፡፡ በተጨማሪም ከጠቅላይ ቤተክህነቱ ለኮሌጁ የተመደበው በጀትም በአግባቡ ጥቅም ላይ እንደማይውልና የሙስና ወንጀል እንደሚፈፀምበት ያነጋገርናቸው ተማሪዎች አክለዋል፡፡
በተለይ ተማሪዎቹ እንደገለፁት ከሆነ የኮሌጁ አካዳሚክ ዲን መምህር ፍስሐፅዮን ደመወዝ እና የቀን ተማሪዎች አስተባባሪ መምህር ዘለዓለም ረድኤት ከቤተክርስቲያኗም ሆነ ከዓለማዊው የመንግስት የትምህርት ተቋም የሌሉ የስነምግባር ጥሰቶች በመፈፀም ተማሪዎችን መሳደብና መምታትን ጨምሮ በማስፈራራት እየዛቱ በመማር ማስተማሩ ሂደት ላይ ችግር እየፈጠሩ ነው የሚል ቅሬታን ሲያቀርቡ ይሰማል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሁለቱም መምህራን ክፍያ የሚፈፀምላቸው ባስተማሩት ኮርስና ክፍለ ጊዜ መሰረት በመሆኑ ዕውቀቱና ልምዱ ያላቸው በርካታ መምህራን እያሉ አብዛኛውን ኮርስ እነሱ ብቻ እየሰጡ ሲሆን በውጤት አሰጣጥ ላይም ችግር እንደሚስተዋልበቻው ተጠቁሟል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በተፈጠረው የአስተዳደር ችግር ምክንያት የምግብ አቅርቦትና ጥራት ችግር በመስተዋሉ ለበላይ አስተዳደሩ ቅሬታ ቢቀርብም ከማስፈራራት ውጭ አዎንታዊ ምላሽ እንዳልተሰጣቸው አስታውሰዋል፡፡
ተማሪዎቹ ካነሷቸው የመብት ጥያቄ ጋር በተያያዘ የ5ኛ ዓመት ደቀመዝሙር ኃይለፅዮን መንግስቱ የተባለ ከማደሪያው በመንግስት የደህንነት ሃይሎች ሌሊት ታፍኖ ተወስዶ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን አካባቢ በሚገኘው ፖሊስ ጣቢያ መታሰሩንና እስካሁንም አለመለቀቁ ተጠቁሟል፡፡
በመጨረሻም ደቀመዛሙርቱ ቅሬታቸውን ለኮሌጁ የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ጢሞቲዎስ ለመንገር ቢፈልጉም አቡኑ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው አርብ መጋቢት 13 ቀን 2005 ዓ.ም. ቅድስት ማርያም መንበረ ፓትርያርክ ወደ ጠቅላይ ቤተክህነት በመሄድ ቅዱስ ፓትርያረኩ ብፁዕ አቡነ ማቲያስን ለማናገር ከቅዳሴ በፊት በስፍራው ብንገኝም ከውጭ አንድ ደህንነት ወደ ውስጥ በመግባት እንዳይወጡ አዟቸው ሳይወጡ ቀርተዋል፡፡ በዕለቱም ፓትርያርኩ እኛን እንዳያናግሩ በመፈለጉ ቅዳሴ እንኳ ሳይገቡ በመቅረታቸው ጥላ ይዘው ሊቀበሏቸው የሄዱ አባቶች ጥላቸውን አጥፈው ሊመለሱ መቻላቸው ተጠቁሟል፡፡ ይሁን እንጂ በነጋታው ፓትርያርኩ ጥቂት የተማሪዎች ተወካዮች እንዲያናግሯቸው ቢጠሩም አቤቱታችንን ከሰሙ በኋላ ምላሻቸው ግን ሄዳችሁ ተማሩ ብቻ ሆኗል ይላሉ ተማሪዎቹ፡፡ ይሁን እንጂ ተማሪዎቹ በድጋሚ ከአባ ሰረቀብርሃን ጋር ባደረጉት ውይይት መጋቢት 18 ቀን 2005ዓ.ም. ትምህርት መጀመራቸው ቢታወቅም አስተዳደራዊና የምግብ ችግሩ ግን እስካሁን እልባት ባለማግኘቱ በግቢው ውስጥ የሚዘጋጅ ምግብ መመገብ አለመጀመራቸው ተጠቁሟል፡፡
በመጨረሻም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የትምህርት ተቋማት የበላይ ጠባቂ የሆኑት አባ ሰረቀብርሃን ኮሌጁ ግቢ ድረስ በመምጣት ካናገሩና የተማሪዎቹ ጥያቄ በቅርቡ ምላሽ እንደሚያገኝና የታሰረው ደቀመዝሙርም በነጋታው ተፈቶ በመምጣት የመማር ማስተማሩ ሂደት እንደሚቀጥል ቃል ከገቡ በኋላ በነጋታው ሲመጡ ቃላቸውን በማጠፍ ጭራሽ ማስፈራሪያና ዛቻ በመፈፀም እንደተመለሱ አዲስሚዲያ ያነጋገራቸው የኮሌጁ ተማሪዎች ገልፀውል፡፡ አባሰረቀ ብርሃን ከዚህ በፊት የማኀበረ ቅዱሳንን ስም በተደጋጋሚ በማጥፋት ተከሰው ዜግነታቸው አሜሪካዊ በመሆኑ ወወደ አሜሪካ በመሄድ ክሱ ተቋርጦ በፊት ከነበሩበት የቤተክርስቲያኗ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ኃላፊነት ተነስተው በአቡነጳውሎስ ፈቃድና መመሪያ የትምህርት ተቋማት የበላይ ጠባቂ እንዲሆኑ መሾማቸውምና በቤተክርስቲያኑ የኑፋቄ ትምህርት አራማጅ ናቸው በሚልም እንደሚጠረጠሩ ይነገራል፡፡
በጉዳዩ ዙሪያ አዲስ ሚዲያ የቤተክርስቲያኗ ቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ የሆኑትን ብፁዕ አቡነ ህዝቄልን ጠይቆ ውሳኔ ለመስጠት ስብሰባ ላይ መቀመጣቸውን ከመግለፅ ያለፈ ምንም ምላሽ ሊሰጡ አልቻሉም፡፡ ከስብሰባው በኋላ የደረሱበትን ውሳኔ ለማጣራትም በድጋሚ ብፁዕ አቡነ ህዝቄል ጋር ስልክ ብንደውልም ስልካቸውን አላነሱልንም፡፡ በኮሌጁ የቀን መርሃ ግብር ትምህርታቸውን እየተከታተሉ የነበሩት ከየ ሀገረስብከቱ የመጡ በአጠቃላይ 180 ደቀመዛሙርት እንደሆኑም ለማወቅ ተችሏል፡፡