የኢትዮጵያ መንግስት ግልፅነትና ተጠያቂነት በሀገሪቱ እንደሚያስፈልግ የተለያዩ ተቋማት በቢሮው ግድግዳ ላይ አሊያም አንድ ለእና በሆነው ኢቴቪ በአመራሮቹ ቢደሰኮርም ከወሬ ባለፈ ሲተገብሩት ግን አይታይም፡፡ በዚህም ምክንያት በሀገሪቱ ግልፅነትና ተጠያቂነት የወሬ ቃልኪዳን እንጂ የተግባር ሲሆን ባለመታየቱ የተለያዩ አስገራሚ ክስተቶች እየተሰሙ ይገኛሉ፡፡ ከነዚህም መካከል የሀገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት የገንዘብ ሙስና ዋነኛው ነው፡፡
ሟቹ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ በገንዘብ በኩል ደሃ ነኝ ሲሉ ከርመው ግብዓተ መሬት ከተፈፀመላቸው በኋላ በ http://www.therichest.org/celebrity networth ዓለም አቀፍ ድህረገፅ አማካኝነት በዓለማችን ካሉ ጠቅላይ ሚኒስትሮች በ 3 ቢሊዮን የአሜሪካድን ዶላር ሁለተኛ ሃብታም መሆናቸውን አነበብን፡፡ ድህረገፁ ይዋሻል እንዳይባል እስካሁን ቅሬታ ያልቀረበበት፣ተዓማኒነትና ተቀባይነት በመኖሩ የተለያዩ የበለፀጉ የዓለም ሀገሮችን ጨምሮ የተለያዩ ሀብታም ነጋዴዎችንና የሀገር መሪዎችን ሃብት መዝግቦ ይፋ ያደርጋል፡፡ በዚህም መሰረት የደሃዋ ሀገር በተለይም ከ12 ሚሊዮን በላይ ህዝቧ በቀን አንድ እንኳ የሚላስ የሚቀመስ ምግብ አጥተው ዜጎቿ በርሃብ የሚሰቃዩበትን አንዳንዶቹም እንደቅጠል በሚረግፉባት ኢትዮጵያ መሪ የነበሩት አቶ መለስ ባለፀጋ መሆናቸውን አበሰረን፡፡
ሰውዬም ሆኑ ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን በፖለቲካ ስልጣን የሀገር መሪ ከመሆናቸው ውጭ ምንም ዓይነት ሃብትም ሆነ የንግድ ስር ዘርፍ እንደሌላቸው እንዲሁም ደሃ ነን ሲሉ ለሀገሬው ህዝብ አዋጅ አዋጅ ማለታቸው በተለያየ ጊዜ በቴሌቪዥን የተናገሯቸው ቃላቶች ምስክሮች ናቸው፡፡ እኛም ያንን አምነን በገንዘብ ደሃ ናቸው ብለን ለማመን ስናገራግር ኸረ ከበርቴ ናቸው የሚል መረጃ ብቅ አለ፡፡የሳቸው ሳያንስ ሰሞኑን ደግሞ የልጃቸው ሰምሃል መለስ የ5 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ቼክ እነሆ እኔም አለሁኝ አለ፡፡
የአቶ መለስ ዜና እና የወ/ሮ አዜብ መስፍን ልጅ የሆነችው ሰመሃል መለስ በአሜሪካ በአንድ ኒዮርክ በሚገኝ ባንክ የ5 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር የምታንቀሳቅስበት ቼክ መገኘቱ በእንግሊዝ ፓርላማ እ.አ.አ. ሐምሌ 10 ቀን 2013 ዓ.ም. (ሐምሌ 2 ቀን 2005 ዓ.ም.)ተገለፀ፡፡ ለዚህም ሰመሃል መለስ ብሩን የምታንቀሳቅስበት ቼክ ቅጂ ነው የተባለውም ከላይ እንደምትመለከቱት በአስረጅነት አብሮ ቀርቧል፡፡ ይህንንም ያቀረቡት በእንግሊዝ አንድ ዩኒቨርስቲ ውስጥ መምህር የሆኑትና የአቶ መለስን አስተዳደር በማስረጃ አስደግፈው እጅግ የሚኮንኑት ዶ/ር ወንድሙ መኮንን ናቸው፡፡
በአሁን ሰዓትም ሰመሃል መለስ 5 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በስሟ ታንቀሳቅሰዋለች ስለተባለው ጉዳይም ጉዳዩ የቀረበለት በእንግሊዝ ፓርላማ የአፍሪካ ጉዳይ ኃላፊ በሆኑት ሚመለከታቸው አካላት የማጣራት ስራ እየተሰራ እንደሆነም እየተገለፀ ይገኛል፡፡ በተለይ የኢህአዴግ አጋር በመሆን፣ ለመለስ አስተዳደር ጥብቅና በመቆምና ለኢትዮጵያም ከፍተኛ እርዳታ በመስጠት የምትታወቀው እንግሊዝ በሰማል መለስ ስም ተቀመጠ የተባለው ብር ትክክለኛ ሆኖ ከተገኘ የራሷን እርምጃ ልትወስድ እንደምትችል ይጠበቃል፡፡
አሁን አቶ መለስ ልጅ ስም ሰነድ(ቼክ) ተገኘ በተባለውም ሆነ የኢህአዴግ ባለስልጣናት ቅዱስ አድርገው የሚስሏቸው አቶ መለስ አላቸው ስለተባለው 3 ቢሊዮን ዶላር የኢትዮጵያው የስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽንም ሆነ እራሱ መንግስት እስካሁን የሰጠው ምላሽም ሆነ ማስተባበያ የለም፡፡ ይህ የሚያሳየው ደግሞ መንግስት አቶ መለስም ሆኑ ልጃው ሰመሃል አላቸው የተባለውን ቢሊዮን ዶላሮች አምኖ ተቀብሏል እንደማለት እንደሆነ እየተነገረ ይገኛል፡፡
በተለይ የህግ ባለሙያው አቶ ዘረሰናይ እንዳሉት ከሆነ የአባትና ልጅ ቢሊዮን ዶላሮች ጉዳይ ደግሞ ሙስናን እታገላለሁ ለሚለው የአቶ ኃይለማርይም አስተዳደር እንዲሁም ለፌደራሉ የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ትልቅ ፈተና ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ ጉዳይ ምላሽ ተነፍጎት የመንደር ሌቦችንና ትናንሽ የመንግስት ሌቦችን እዣለሁ መባሉ ከእንግዲህ የሚታመን እና የሚዋጥ እንደማይሆን አስተያየቶች እየተሰጡ ይገኛሉ፡፡
መንግስት በበኩሉ ከእንግዲህ ሙስናን ለመዋጋት መታገስ አይገባኝም ቢልም ሰርዓቱ በራሱ የሙስና ተግባር ላይ መሰረት ያደረገ በመሆኑ መያዝ የሚገባቸውን ጨክኖ አይዝም በሚል ይታማል፡፡ ከፌደራሉ የመንግስት ሰራተኞች በተጨማሪ በክልሎች ላይ ስልጣናቸውን ተገን በማድረግ ሙስና የሚፈፅሙ የመንግስት ሰራተኞች ላይ በቅርቡም በኦሮሚያ ክልል እርምጃ መወሰድ መጀመሩን እሰየው፣ በሌሎችም በሁሉም ክልሎች ተጠናክሮ ይቀጥል የሚሉ እንዳሉ ሁሉ የለም ህዝብ የሚያውቃቸው ባለስልጣናት እስካልተያዙ ድረስ በዚህ መፎከር ተገቢ አይደለም የሚሉ አልታጡም፡፡
በተለይ ሰሞኑን የአቶ መለስ ልጅ አላት በተባለው ገንዘብ ዙሪያ እሳ የየትኛውም መንግስት ሰራተኛም ሆነ ነጋዴ ስላልሆነች የገንዘቡ ትክክለኛነት ከተረጋገጠ ወላጆቿ ስልጣናቸውን አላግባብ በመጠቀም ከህዝብ የዘረፉት ስለሚሆን ጉዳዩ ትኩረት ተሰጥቶት ምላሽ ሊቸረው እንደሚገባ እየተጠቆመ ይገኛል፡፡ ይህም የተለያዩ የማኀበራዊ ድህረ-ገፆች ላይ በስፋት መወያያ እየሆነ መገኘቱ ጉዳዩ ይበልጥ ትኩረትን ስቧል፡፡ ይህንንም ተከትሎ መንግስት በተለይ ከዳያስፖራ የአባይ ግድብን ጨምሮ ለተለያዩ ፕሮጀክቶች ማስፈፀሚያ ድጋፍ ቢጠይቅ እንኳ አሉታዊ ተፅዕኖ ይኖረዋል፡፡ ዓለም አቀፍ ለጋሾች ምንም እንኳ ሁልጊዜም ቢሆን ድጋፍ ሲያደርጉ ከሀገሮቹ ይልቅ የራሳቸውን ጥቅም ታሳቢ ቢያደርጉም ለኢትዮጵያ የሚሰጠው እርዳታና ብድር ለባለስልጣናቱ ኪስ ማደለቢያ ነው በሚል የራሳቸውን እርምጃ እንዲወስዱ እንዲህ ዓይነቱን መረጃ የሰሙ ዜጎቻቸው ለኢትዮጵያ የሚደረገውን ድጋፍ በመቃወም አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደራቸው አይቀርም፡፡
ምንጭ፡- ኢቦኒ መፅሔት