የቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት እና የአሁኑ የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ(አንድነት) ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ታሰሩ፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ የታሰሩት ዛሬ መስከረም 15 ቀን 2006ዓ.ም. አንድነት ፓርቲ አባላት በጉለሌ ክፍለ ከተማ መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም. በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ለተጠራው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በሽሬ ሜዳ ቅስቀሳ በማድረግ ላይ ሳሉ መታሰራቸውን ተከትሎ የፓርቲው ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ያዘዝኩት እኔ ስለሆንኩ ልጆቹን ልቀቁ፤ ከፈለጋችሁ እኔን ማሰር ትችላላችሁ በማለታቸው የጣቢያው ፖሊሶችme ዶ/ሩ ነጋሶን ማሰራቸው ተረጋግጣል፡፡
በአሁን ሰዓት የማዘዣው ፖሊሶች ዶ/ር ናጋሶን ከያዙበት ሽሬሜዳ ወደ ጉለሌ ፖሊስ መምሪያ በፖሊስ መኪና እና በበርካታ ፖሊሶች ታጅበው ተወስደዋል፡፡ እስካሁንም ዶ/ሩ ነጋሶን በፖሊስ መመሪያው የማዘዣው ፖሊሶች ከማድረስ ውጭ ያነጋገራቸው ፖሊስ የለም፡፡ በቅስቀሳ ላይ እያሉ የታሰሩትና ዶ/ር ነጋሶ ሊያስፈቱ ሄደው በምትካቸው በመታሰራቸው የተለቀቁት የአንድነት ፓርቲ አባላትም ቅስቀሳቸውን የቀጠሉ ሲሆን ሌሎች አባላትም እሁድ መስከረም 19 ቀን 2006ዓ.ም. በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ለሚደረገው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ እያደረጉ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ዘግይቶ በደረሰን የተያያዘ ዜና በዚሁ በአዲስ አበባ በቅስቀሳ ላይ ያሉት የአንድነት አባላት 16 አባላት ታስረዋል፡፡ በዚህ ጉዳይም ሌሎች የአንድነት ፓርቲ ከፍተኘኛ ስራ አስፈፃሚ አመራሮች የታሰሩ አባላቱን ለማስፈታት ወደየ አካባቢው አቅንቷል፡፡