አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ (አንድነት) ፓርቲ የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት በሚል መሪ ቃል የ3 ወር ህዝባዊ ንቅናቄ ፍፃሜ በአዲስ አበባ ዛሬ መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም. በተካሄደ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተጠናቀቀ፡፡ ፓርቲው ከሰኔ ወር ጀምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ መካከል በደሴ፣ በጎንደር፣ በአርባምንጭ፣ በጂንካ፣ በባህርዳር፣ በአዳማ(ናዝሬት)፣ በባሌ ሮቤ፣ በፊቼ እና በመቀሌ ከተሞች የተቃውሞ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ የጠራ ቢሆንም በባሌ ሮቤና በመቀሌ ከተማ በገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ ሲሰናከል ቀሪዎቹ በሙሉ በስኬት መጠናቀቃቸው ይታወቃል፡፡
የመርሃ ግብሩን ፍፃሜ መስከረም 3 ቀን 2006 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ለማድረግ ሰፊ እንቅስቃሴ ቢደረግም የከተማው መስተዳደር በበኩሉ የተለያዩ ምክንያቶችን በመጥቀስ ሰልፉ ወደ መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም. እንዲዛወርለት በጠየቀውና እውቅና በሰጠው መሰረት ባለፈው ሳምንት ቅስቀሳ እየተካሄደ ነበር፡፡ በቅስቀሳው ላይ የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ፣ በፓርላማ ብቸኛው የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ ተወካይና የአንድነት ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ግርማ ሰይፉን ጨምሮ ስራ አስፈፃማና አባላት ቅስቀሳ ሲያደርጉ ለ3 ተከታታይ ቀናት በፖሊ መታገታቸው አይዘነጋም፡፡ ይሁን እንጂ ፓርቲው ከ33 ቱ ፓርቲዎች ጥምረት ጋር በጋራ በመሆን የዛሬውን የተቃውሞ ሰላማዊ ሰለፍ ሲያስተባብር ቢቆይም የሰልፉ መዳረሻ ቦታን ግን መስተዳደሩ ከፓርቲው ፍላጎትና ያቄ ውጭ በጃንሜዳ እንዲደረግ ቢወስንም ፓርቲው መስቀል አደባባይ ለማድረግ መወሰኑን ተከትሎ ቅስቀሳው ተካሂዷል፡፡
ፓርቲው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉን ከፓርቲው ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ቀበና መድኃኔዓለም ፊት ለፊት ከሚገኘው ዋና ፅህፈት ቤት በመጀመር ወደመስቀል አደባባይ ሊያመራ ሲል በ4 ኪሎ መስቀል አደባባይ ወደሚያመራው በሙሉ በበርካታ ፖሊሶችና በሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ሊገታ ችሏል፡፡ በመጨረሻም የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች፣አባላትና ደጋፊዎች እስከ 4፡50 ሰዓት ድረስ ባሉበት ቦታ ከከተማ መስተዳደሩና ደብዳቤ ከተፃፈላቸው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ምላሽ አልተገኘም፡፡ የዝግጅት ክፍሉም የእገታውን ምክንያት ለማጣራት የከተማው ከንቲባ ድሪባ ኩማ፣ ምክትላቸው አቶ አባተ ስጦታው፣ የመንግስት ኮሞኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር ተደጋጋሚ ስልክ ብንደውልም ስልካቸውን በመዝጋታቸው ሐሳባቸውን ማካተት አልቻልንም፡፡
ይሁን እንጂ የአቶ ሬድዋን ምክትል ወደሆኑት አቶ ሽመልስ ከማል ጋር ብንደውልም ስልካቸውን በተደጋጋሚ ሊያነሱልን አልቻሉም፡፡ የፖሊስ ኃላፊዎች በበኩላቸው እገታ እንዲያደርጉ ትዕዘዝ ከመቀበል ውጭ እኛም ምክንያቱን አናውቅም የሚል ምላሽ የሰጡ እንዳሉ ሁሉ ምክንያቱን ሲጠየቁ ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ ያልሆኑም አልታጡም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተለያዩ አካባቢዎች በተለይም መስቀል አደባባይ፣ ሜክሲኮ፣ አስኮ፣ ፒያሳ፣ሳሪስ፣መርካቶ፣ኮተቤና በሌሎች አካባቢዎች ያሉ ሰዎች ሰልፉ ወደዳለበት ቀበና እንዳይሄዱ ፌደራል ፖሎስን ጨምሮ በአዲስ አበባ ፖሊሶች መታገቱን ለማየት ችለናል፡፡ በሰልፉ ላይ ከተሰሙ መፈክሮች መካከል እነ አንዱዓለም አራጌ፣አቶ በቀለ ገርባ፣ አቶ ናትናኤል መኮንን፣አቶ ኦልባና ሌሊሳ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ፣ የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ከሚቴዎች እነ አቡበከር የነፃነትና የመብት ጠያቂዎች እንጂ አሸባሪዎች አይደሉም፣ የፀረ-ሽብር ህጉ የህገመንግስት ጥሰት ነው፣ ለኑሮ ውድነቱ መንግስት ተጠያቂ ነው፣ህገመንግስቱ ይከበር፣ ውሸት ሰልችቶናል፣ለአምባገነኖች አንበረከክም የሚሉ ይገኙበታል፡፡
በመጨረሻም ሰላማዊ ሰልፉ ቀበና አደባባይ አካባቢ ወደ መገናኛም እንዳይሄድ ከፊትና ከኋላ በፖሊስ እገታ በመፈፀሙ የመርሃ ግብሩ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ አቶ ትዕግስቱ አወሉ፣ የ33ቱ ፓርቲዎች ተወካይ አቶ ግርማ በቀለ እንዲሁም የአቶ አንዱዓለም አራጌ ፣ የአቶ በቀለ ገርባ እና የሌሎች የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞች ከቃሊቲና ከዝዋይ እስር ቤቶች የተላከ ደብዳቤ ከተነበበ በኋላ ከቀኑ 6፡30 ሰዓት ላይ ከ80 ሺህ በላይ ሰዎች በተገኙበት ሰልፉ በታገተበት ቀበና አደባባይ ፊትለፊት በስኬት ተጠናቋል፡፡