ቀደም ሲል መስከረም 23 ቀን 2007 ዓ.ም. ለምሳ ሲወጡ ቢሯቸው ታሽጎ ሰኞ መስከረም 26 ቀን 2007 ዓ.ም. የተከፈተው እና ለሰባት ሳምንታት ህትመቷ የተቋረጠው የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ወርቁ በፌደራል የወንጀል ምርመራ ማዕከል ማዕከላዊ ፖሊስ ቃሉን እንዲሰጥ በተደረገለት ጥሪ መሰረት ማክሰኞ መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ማዕከላዊ መቅረቡ ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛው ማዕከላዊ የተጠራው የቀድሞው መኢአድ አመራር የነበረው አቶ ማሙሸት አማረ ክስ መሰረት ቃሉን እንዲሰጥ የነበረ ቢሆንም፤ ማዕከላዊ ምርመራ ክፍልም የጋዜጠኛውን ቃል ከተቀበለ በኋላ ጉዳዩ አስፈላጊ ሲሆን እንደሚቀርብ በመጠቆም በ5,000.00 (አምስት ሺህ ) ብር ዋስ መለቀቁ ተጠቁሟል፡፡
ኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ መንግስት በጋዜጠኞች፣ በመፅሔቶች እና ጋዜጦች ላይ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የሚወነጅል ዘጋቢ ፊልም በተደጋጋሚ መስራቱን ተከትሎ አታሚ ቤቶች የነፃ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን እንዳያትሙ በተለያዩ የመንግስት አካላት ጫና በማሳደሩ ለ7 ሳምንታት ከህትመት መቋረጧን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የጋዜጣው አዘጋጆች በተደጋጋሚ ስራውን አጠናቀው ቀድም ሲል የሚያትምላቸው አታሚ ድርጅትና ሌሎች አታሚዎች ጋር በተደጋጋሚ ቢኬድም እስካሁን ለማተም ፈቃደኛ እንዳልሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ መንግስት የነፃ መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞችን፣ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን በተደጋጋሚ መወንጀሉ እና መክሰሱን ተከትሎ የተለያዩ በርካታ ነፃ ጋዜጦችና መፅሔቶች ከህትምት እና አንባቢ ውጭ እንዲሆኑ መደረጉ ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ከሚያዝያ 2006 ዓ.ም. እስከ ነሐሴ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ ድረስ ከ25 ያላነሱ የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች የግፍ እስርና ስቃዩን በመሸሽ መሰደዳቸው ይታወቃል፡፡ በአሁን ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ 3 የውጭ ዜጎችን ጨምሮ ከ17 ያላነሱ ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች በግፍ ታስረው ይገኛሉ፡፡
፡