አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ከታህሣሥ 3-4 ቀን 2007 ዓ.ም. ያደረገው አስቸኳይ ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ ተጠናቀቀ፡፡ ፓርቲው በተከታታይ ቀናት መዋቅሩን ከዘረጋባቸው ከአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫዎች በመጡ አባላቱ ባደረገው ልዩ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔ የተለያዩ አጀንዳዎችን በማፅደቅ ውሳኔዎችን ያሳላፈ ሲሆን፤ በተለይም የቀድሞው የፓርቲው ፕሬዘዳንት ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው በገዛ ፈቃዳቸው ስልጣናቸውን ከለቀቁ በኋላ በፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት የተመረጡትን ፕሬዘዳንት አቶ በላይ ፈቃዱን ስልጣን ከነ ስራ አስፈፃሚዎቹ አፅድቋል፡፡ ሌላው ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የጠቅላላ ጉባዔ አባላትን ቁጥር በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ በአባላቱ ተወስኖና የፀደቀው ደንቡ ላይ ሰፍሮ ይቅረብልኝ ባለው መሰረት ተወስኖ እንዲሰፍር መደረጉ ተጠቁሟል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከዋና አጀንዳዎቹ መጠናቀቅ በኋላ ፓርቲው በአመራር አባላቱ ለጠቅላላ ጉባኤ አባላት በሀገሪቱ ነባራዊ ሁኔታዎች(የአርሶ አደሩ ፤የከተማው ነዋሪ፤የባለሐብቱ ሁናቴ) በዳግማዊ ተሰማ፣ የተማሪውና የምሁሩ ነባራዊ ሁኔታ በጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ፣ የአንድነት የምርጫ ስትራቴጂ ግብ በፓርቲው ፕሬዝዳንት አቶ በላይ ፈቃዱ መቅረቡ ታውቋል፡፡
በመቀጠልም የስልጠናው ተሳታፊዎች ጥያቄና አስተያየት በመስጠት ስልጠና ተጠናቆ፣ በፓርላማ ብቸኛው የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካይና የአንድነትፓርቲምክትል ፕሬዝዳንት የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ በምርጫ ስትራቴጂ ዙሪያ ስልጠና ሰጥተዋል፡፡አባላቱ የፓርቲው የህግና ሰብአዊ መብት ጉዳይ ምክትል ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ገበየሁ ይርዳው የአባላት መብትና ግዴታ ከፓርቲው ደንብና ከፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ አንጻር ስልጠና ከሰጡ በኋላ መድረኩ ለውይይት ክፍት ሆኖ በስልጠናዎቹና ወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት መደረጉን የደረሱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በመጨረሻም የፓርቲው ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክሌ በቀለ የጉባኤውን የመዝጊያ ንግግር በማድረግ አንድነት በብሔርም ሆነ በህብረብሔር ፓርቲዎች ጋር አብሮ ለመስራት መዘጋጀቱንና ከአንድነት ፓርቲ ጋር ተመሳሳይ የፖለቲካ ፕሮግራም ላላቸው ፓርቲዎች ሁሉ የውህደት ጥያቄ ማቅረባቸው ተጠቁሟል፡፡ አቶ ተክሌ አንድነት ፓርቲ የ2007 ዓ.ም. ምርጫን በአሸናፊነት ለመወጣት እየሰራ እንደሚገኝና አባላቱም በያሉበት ጠንክረው የበኩላቸውን እንዲወጡ በማሳሰብ ጉባዔው በስኬት መጠናቀቁን ፓርቲው አስታውቋል፡፡