የገዥው ፓርቲ ቀኝ ዕጅ ተደርጐ የሚወሰደው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በዛሬው ዕለት ለፓርቲዎች የሚሰጠውን የፋይናንስ ድጋፍ ክፍፍልን አስመልክቶ በምርጫ ከሚወዳደሩ ሀገር-አቀፍ ፓርቲዎች ጋር የጠራው የውይይት ሀሳብ ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ውድቅ ተደረገ፡፡ ቦርዱም ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሞታል፡፡
በግዮን ሆቴል ጉባዔ አጠቃላይ ከ25 በላይ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የተገኙ ሲሆን ቦርዱ ፍትሐዊ ያለውን የፋይናንስ ክፍፍል ቀመር አቅርቧል፡፡ በዚህም መሠረት ለእኩልነት መስፈርት 10% ፣ የፓርላማና የክልል ም/ቤት መቀመጫን መሰረት ያደረገ የፍትሐዊነት መስፈርት 55%፣ ባቀረቡት የእጩዎች ብዛት 25% እና የሴት እጩዎች ብዛት 10% በሚል ቀመር ቢያቀርብም ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ መልኩ እና በኢህአዴግ እንደ አጋር የሚታዩ ፓርቲዎች ሳይቀር በሙሉ ድምፅ “ኢህአዴግን ዳግም ለማንገስ የተሰራ ቀመርና የቦርዱን ገለልተኛነት ጥያቄ ያጋለጡ” በማለት ከፍተኛ ትችትና ተቃውሞ እንደቀረበበት አንድነት ፓርቲን ወክለው በቦታው የተገኙት አቶ ዳንኤል ተፈራ፣ ገልፀዋል፡፡
አንድነት በመወከል ስብሰባው ላይ የተሳተፉት የአንድነት ተወካይ አቶ ዳንኤል ተፈራ፣ እንደገለፁት “ስብሰባው ላይ ምርጫ ቦርድ ላይ የቀረበበት ውግዘትና ያቀረበው ቀመር ከኢህአዴግ ተወካይ በስተቀር የሚደግፈው ማጣቱ እንዲሁም ስርዓቱን ኢህአዴግ ይደግፍኛል ብሎ የሚተማመንባቸው ፓርቲዎች ከጉያው እየወጡ እንደሆነ የሚጠቁም አጋጣሚ ነው” ሲሉ ገልፀዋል፡፡ አያይዘውም ተሳታፊዎች ምርጫ ቦርድ ስብሰባዎችና ሀሳቦችን ከዜና ማድመቂያነት ባለፈ በተግባር ለውጦ እንዲያሳይ እና ሀገራዊ ግዴታውን እንዲወጣ በርካታ ማሳሰቢያዎች የቀረቡ ሲሆን ዳግመኛ በታሪክ ቅሌት እንዳይወድቅ ከአድሏዊ አሰራር ራሱን እንዲያላቅቅ ምክርም ተለግሶታል፡፡
በተለይም ፓርላማና የክልል ም/ቤት ባለ መቀመጫ በሚል የተመደበውን ገንዘብ በኢህአዴግ ለማስረከብ መዘጋጀቱ ተቀባይነት እንደሌለውና እንደገና ራሱን እንዲፈትሽ አብዛኛው ተሳታፊ ገልፆል፡፡
ቦርዱ ቀመሩን የሰራሁት ከ111 ሀገሮች ተሞክሮ ወስጄ ነው ቢልም፡፡ ተሳታፊዎቹ የሌሎች ሀገሮች ተሞክሮ እና የኢትዮጵያ ተሞክሮ የሚለያይ ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ገዥ ፓርቲ ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ የማይጨነቅ፣ ተቃዋሚዎችን ለማጥፋት የሚሰራና የይስሙላ ምርጫ የሚያደርግ በመሆኑ ለንፅፅር የሚቀርብ አይደለም ስለዚህ ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ተነስተን ቀመሩን እናውጣ በማለት ምርጫ ቦርድ ያቀረበው የፋይናንስ ክፍፍል ቀመር ውድቅ ተደርጐበታል፡፡
በምርጫ ቦርድ የቀረበውን የፋይናንስ ድጋፍ ክፍፍል ተገቢ ነው የሚል ድጋፍ የሰጠው የኢህአዴግ ተወካይ ብቻ ሲሆን ሌሎች ተሳታፊዎች ተቃውሞ በማሰማትና ቀመሩን ባለመቀበል ኢህአዴግ ብቻውን የቆመበት ስብሰባ ነበር ሲል የአንድነት ፓርቲ ተወካይ አቶ ዳንኤል ተፈራ ተናግሯል፡፡ በመጨረሻም ቦርዱ የቀረበበትን ተቋም ከግምት አስገብቶ የፋይናንስ ክፍፍል ቀመሩን አስተካክሎ እንደሚቀርብ ይጠበቃል፡፡
ምንጭ፡ ፍኖተ ነፃነት