ዛሬ ቅዳሜ ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም. ከረፋዱ 5 ሰዓት ላይ ከቶጎ ሎሜ ተነስቶ ጋና አክራ ይጓዝ የነበረው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 737-400F ዕቃ ጫኝ አውሮፕላን ተከሰከሰ፡፡ አውሮፕላኑ አደጋ የደረሰበት በመጥፎ የአየር ፀባይ መሆኑን በመጥቀስ አብራሪው በጋና ኮቶካ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በሰላም ለማሳረፍ ጥረት በሚያደርግበት ወቅት መሆኑ የጋና አየር ማረፊያ ኮሚኒኬሽን ኦፊሰር ኒውማን ኳርቴይ ተናግረዋል፡፡
ኦፊሰሩ እንደተናገሩት ከሆነ የበረራ ቁጥር ET –AQV46 መሆኑን ጠቅሰው፤ የአውሮፕላኑ አብራሪን ጨምሮ በውስጡ የነበሩ 3 ሰራተኞች ከአደጋው ህይወታቸው መትረፉንና በጋና 37 ሚሊተሪ ሆስፒታል የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በአደጋውም 3ቱ ሰረተኞች የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደሆነ ከመግለፅ በስተቀር ከአውሮፕላኑ መከስከስ በስተቀር በሌላ የሰው ሕይወት ላይ ያስከተለው ጉዳት ስለመኖሩ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ የተገለፀ ነገር የለም፡፡
አደጋው የደረሰበት የጋና አክራ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያም የሀገሪቱ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች የጦር ኃይል፣ፖሊስ፣ የደህንነትና የአቭየሽን ባለስልጣን በአካባቢው ተገኝተው ከሚያደርጉት ማጣራት በስተቀር መደበኛው ስራ መቀጠሉን ማረጋገጣቸውን የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡