ብስራት ወልደሚካኤል
ከዚህ በፊት ኢህአዴግ ጠንካራ የሰላማዊ የፖለቲካ ታጋይ አመራሮችንና አባላቱን አሰረ፡፡ በመቀጠልም ጋዜጠኞችና የዞን 9 ብሎገሮችን አሰረ፡፡ ይህም አልበቃ ሲለው አሁን ደግሞ በራሱ ምርጫ ቦርድ ተወዳድረን እናሸንፍሃለን ብለው የቆረጡ ተፎካካሪዎችን ከምርጫ ለማስወጣት ባትሏል፡፡ ለዚህም ማሳያ አንድነት ፓርቲን አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባዔ ጥሩ ምናም…መኢአድን ደግሞ እናንተም ችግር የውስጥ ችግራችሁን ፍቱ፣…ሰማያዊ ፓርቲን ደግሞ ምርቻ ቦረድ በጠራው ስብሰባ ላይ ረግጣችሁ ጥታችኋልና ይቅርታ ካልጠየቃችሁኝ፣…ኃይማኖታዊ በዓል በሆነውና ከጥር 10-12 በሚከበረው የጥምቀት በዓል ዋዜማና ስነስርኣት ሰማያዊ ልብስ እንዳይለበስ የሚል ትዕዛዝ መስጠት፣…ዛሬ ደግሞ ለነገ ጠቅላላ ጉባኤ የጠራውን አንድነት ፓርቲ ላይ ለመሳተፍ የተንቀሳቀሰውን የአንድነት ፓርቲ የምስራቅ ቀጠና አደራጅ አዳማ/ናዝሬት ላይ ማገት፣…እያለ ጠንካራ የተባሉ የተፎካካሪ ፖለቲካ አባላትንና አመራሮችን ማገትና ማሰሩን ቀጥሏል፡፡ ከዚህ በፊት ከ200 ያላነሱ ጠንካራ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣አባላት፣ጋዜጠኞች፣ብሎገሮችንና አክቲቪስቶችን በግፍ ማሰሩ አይዘነጋም፡፡
በርግጥ ኢህአዴግ ድሮም ፈሪ ነው፡፡ የሚፈራው የኢትዮጵያን ህዝብ ብቻ ሳይሆን፤ ሐሳብን በራሱ ይፈራል፡፡ ለዚህም ነው ከእስክሪብቶና ወረቀት ውጭ በእጃቸው ምንም የሌላቸውን ንፁሃንን አሸባሪ እያለ ሚያስረው፡፡ አምባገነንቱና ጨካጭነጹ ከፍርሃትና ከድንቁርና የመኘጨ እንጂ የፖለቲካ ስትራቴጂ ሆኖ አይደለም፡፡ ይህ ግን በስልጣን ለመቆየት ዋስትና ሊሆን አይችልም፤ሆኖም አያውቅም፡፡ ይልቅ ጭቂና እና ጭካኔ በገዥዎች በተበራከተ ቁጥር ገና ወደፊት ይመጣል ተብሎ የተፈራውን ህዝባዊ አብዮት ራሱ ኢህአዴግ እያቀረበ ያለ ይመስለኛል፡፡ ምንም እንኳ የምርጫ እንቅስቃሴ መኖሩና ተፊካካሪዎች ወደ ውድድሩ ቢገቡ እንደ አንድ መልካም ነገር ቢታይም፤ ምርጫው ላይ ከበፊቱ የተለየ ውጤት ይኖራል ተብሎ ላይጠበቅ ይችላል፡፡ የምርቻ ሂደቱ በራሱ ግን ህዝቡን የፖለቲካ መብቱን እንዲጠይቅና እንዲጠቀም ከማድረግ አኳይ አዎንታዊ ሚና መኖሩ እሙን ነው፡፡
ህዝባዊ አብዮት ምንጊዜም የሚፈጠረው በገዥዎች ምክንያት ድንገት እንጂ በህዝቡ ታቅዶና ተፈልጎ አይደለም፡፡ ህዝቡ የአብዮቱ ምክንያት በሆኑ ገዥዎች ህዝባዊ እምቢተኝነት አንዱ አፀፋ ምላሽ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ በርካታ የጦር መሳሪያ አለኝ ብሎ በአፈሙዝ አስቦና ተመክቶ ህዝባዊ አብዮትን ቢፈራም በራሱ ጊዜ እያፈጠነውና እየጠራው ያለ ይመስለኛል፡፡
አሁን ግን ኢህአዴግ ምርጫ ቦርድን፣ ፍርድ ቤትን፣ ደህንነትን፣ ፖሊስን፣ መከላከያን፣ሚዲያውን እና ኢኮኖሚውንም ይዞ ሊረጋጋ አልቻለም፡፡ የሚገርመው ህዝባዊ ደጀን ከጀርባቸው እንዳለ በማመን እስክሪብቶ፣ወረቀትና ሐሳብ የያዙትን ከጦር በላይ መፍራቱ እርግጥ ነው፡፡ ግን በመፍራት፣ ጭካኔና ኃላፊነት በጎደለው ስሜት የሚወሰዱ እርምጃዎችን ከፈሩት ነገር ለማምለጥ ዋስትና ከመሆን ይልቅ የፈሩትን ነገር የማምጣት ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡
ኢህአዴግ አሁን እያደረገ ያለው የእውር ድንብር ተግባሩ በራሱ ጊዜ የፈራውን ህዝባዊ አብዮት ከምን ጊዜውም በላቀ ሁኔታ እየጠራው ነው፡፡ ይሄም በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች፣አባላትና አመራሮች፣ በአክቲቪስቶችና ጋዜጠኞች ሳይሆን በራሱ በኢህአዴግ የከበረ ጥሪ እየተደረገለት ነው፡፡ በርግጥ ህዝባዊ አብዮት ድንገት የሚፈጠር ህዝባዊ አመፅ/እምቢተኝነት በመሆኑ አምባገነኖችን ድንገት ሳያስቡ ከስልጣን በማውረድ በበጎ ጎኑ ቢታይም የጦርነት ውጊያን ያህል ባይሆንም የሰው ህይወትና ንብረት ላይ ጉዳት ማድረሱ አይቀርም፡፡ ነገር ግን ራሳቸው አምባገነኖች በሚፈጥሩት ቅጥ ያጣ ጭቆና የሚመጣ በመሆኑ በፀጋ ከመቀበል ውጭ ሌላ አማራጭ ያለ አይመስለኝም፡፡ እነደ ሌሎቹ ስልጡናን የመንግስት ስርዓት ከጦርነት ክህዝባዊ አብዮት ይልቅ በሰለጠነው ነፃና ፍትሃዊ በሆነ የህዝብ ምርጫ ቢሆን መልካም ነበር፡፡ ነገር ግን የዚህ ሁሉ ዕድል ከተዘጋ የታፈነ ህዝብ ነገ ባልታሰበ ጊዜ ህዝባዊ እምቢተኝነት ወይም አመፅ ውስጥ መግባት አይቀሬ ነው፡፡ ለዚህ ተጠያቂ ደግሞ ራሱ ኢህአዴግና የበኩር ልጁ ምርጫ ቦርድ መሆናቸውን ማወቅ አለባቸው፡፡
አሁን አብዮቱን እየጠራ ያለው ኢህአዴግ ብቻ ሳይሆን ልጁ ታማኝ ልጁ ምርጫ ቦርድ በመሆናቸው በሀገሪቱና በህዝቡ ላይ ለሚፈጠሩ ጥፋቶች ተጠያቂዎቹ ተቋማቱ ብቻ ሳይሆኑ የኢህአዴግ አመራሮችና የምርጫ ቦርድ ዋና አመራሮችና እንደ የደረጃቸው ሌሎች የቦርዱና የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚዎች እንደየስራቸው ከተጠያቂነት ማምለጥ እንደማይችሉ ከወዲሁ ራሳቸውን መመርመርና የዓለማችንና የህዝባንን ነባራዊ ሁኔታ መገንዘብ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡ አለበለዚያ እንደ ከዚህ ቀደሙ በንፁሃን ደም ነግዶ መኖርና ማላገጥ፣ ሀገርና ትውልድ አጥፍቶ አመልጣለሁ ማለት የማይቻልበት ጊዜ ላይ መድረሳችንንም ሊረሳ አይገባም፡፡ ስለዚህ በሀገሪቱ ላይ እስካሁን ከፈፀሙት በደል በተጨማሪ አሁንም ለመፈፀም ለተዘጋጁ ጥፋቶች ምርጫ ቦርና ኢህአዴግ ከነተባባሪዎቻቸው መቼም ቢሆን ከተጠያቂነት እንደማያመልጡ መረዳት አለባቸው፡፡ ምንክንያቱም እንደከዚህ ከቀደሙ በዝምታም ሆነ በፍራቻ የሚታለፍበት ጊዜ አልፏልና፡፡ ምናልባት ለመተንበይ አስቸጋሪ ቢሆንም በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርዓት ለውጡ የማይቀር እውነት ነው፡፡
መቼም በአሁን ጊዜ እንደቀድሞ በተጭበረረበር ምርጫና በካድሬ ውዳሴ ከንቱ ዳንኪራ ምርጫ አድርጌ አሸንፊያለሁ ማለት ለምርጫው የወጣውን ወጪ ከየትኛውም የኢኮኖሚ ኪሳራ በላቀ አጉልቶ ከማሳየት በስተቀር በስልጣን ለመቆየት ዋስትና ሊሆን አይችልም፡፡ ምርጫ አንዱ የዴሞክራሲያዊ የመነግስት ስርዓት ሽግግር መገለጫ እንጂ ብቸኛው ህዝብን የስልጣን ባለቤት ማድረጊያና አምባገነኖችን ከሚንደላቀቁበት ስልጣን ማስወገጃ መንገድ አይደለም፡፡ ይሄ ደግሞ ከማንም የሚሰወር አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ባይኖሩ እንኳ በርካታ የሰላማዊ ትግል ስልቶች እንደየወቅቱ፣እንደየሀገሩና ህዝቡ የሚተገበሩ አሉና፡፡ ስለሆነም መጪውን ጊዜ ስለሀገራችን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ በተለይም የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሚደረገው ምርጫ ሂደትና ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ይፋ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ውጤት ከወዲሁ በጉጉት እንድንጠብቀው ግድ ብሎናል፡፡