አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በመጪው ምርጫ ግንቦት 2007 ዓ.ም. ለመሳተፍ መወሰኑን እና ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩ 450 ዕጩዎቹን በአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫ ማቅረቡን ይፋ ካደረገ በኋላ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በድጋሚ ጠቅላላ ጉባዔ አድርጎ የፓርቲውን ፕሬዘዳንቱን ካለተመረጠ ምርጫው ላይ እንዳይሳተፍ አደርጋለሁ ባለው መሰረት ዛሬ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባ ቀበና በሚገኘው የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት አዳራሽ ጠቅላላ ጉባዔው መካሄዱ ታውቋል፡፡ ፓርቲውን ለመምራት በዕጩነት ቀርበው የተወዳደሩት አቶ በላይ ፈቃዱ፣ አቶ አለነ ማህፀንቱ እና አቶ ዳግማዊ ተሰማ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ለፕሬዘዳንትነት የተወዳደሩት ሶስቱም ዕጩዎች በወጣትነት የዕድሜ ክልል ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ በትምህርታቸው የማስተርስ ድግሪ፣ በፖለቲካ ተሳትፎ ሶስቱም በአንድነት ፓርቲ በተለያየ ከፍተኛ አመራርነት ያገለገሉ ሲሆን፣ በሙያቸውም የተለያዩ ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ተቋማት ላይ ማገልገላቸው ተጠቁሟል፡፡ በመጨረሻም በነበረው ውድድር አቶ አለነ ማህፀንቱ ራሳቸውን በገዛ ፈቃዳቸው ከውድድሩ ውጭ በማድረግ በአቶ በላይ ፈቃዱና በአቶ ዳግማዊ ተሰማ መካከል በተደረገ የምረጡኝ ቅስቀሳና ውድድር የጠቅላላ ጉባዔው አባላት ባደረጉት የምስጢር ድምፅ አሰጣጥ መሰረት አቶ በላይ 183 ድምፅ በማግኘት የአንድነት ፕሬዘዳንት ሆነው ተመርጠዋል፡፡ አንድነት መተዳደሪያ ደንብ መሰረት የጠቅላላ ጉባዔው አባላት 320 ሲሆን፤አቶ በላይም የአባላቱን 57.2 በመቶ ድምፅ በማግኘት አሸንፈዋል፡፡
ውጤቱን ተከትሎም ተፎካካሪያቸው የነበሩት አቶ ዳግማዊ ተሰማ ለአቶ በላይ ፈቃዱ የእንኳን ደስ ያሎት መልዕክት በማስተላለፍ መጪውን ምርጫ አንድነት ፓርቲ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ በጋራ ጠንክረው መስራት እንዳለባቸውና ለዚህም በፓርቲው የሚሰጣቸውን የስራ ድርሸና ተልዕኮ ለመወጣት ዝግጁ እንደሆኑ መግለፃቸውን ከስፍራው የአዲስሚዲያ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በመጨረሻም አቶ በላይ ፈቃዱ ፓርቲውን በፕሬዘዳንትነት ለመምራት ቃለ መሐላ መፈፃማቸው ታውቋል፡፡
በጉባዔው ላይ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማቶችና ጋዜጠኞች እንዲሁም ሌሎች ተጋባዦች የተገኙ ሲሆን፤ በሀገሪቱ የምርጫ ቦርድ ህግ መሰረት ሂደቱን መታዘብ የነበረበት ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሂደቱን ለመታዘብ እንደማይገኝና ወኪልም እንደማይልክ ቀደም ሲል ከፓርቲው ለተደረገለት ጥሪ በደብዳቤ ማሳወቁ ተጠቁሟል፡፡ ቀደም ሲል ታህሳስ 2006 ዓ.ም. የፓርቲው ፕሬዘዳንት የነበሩት ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው ስልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው በመልቀቅ ለፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት ካስረከቡ በኋላ አቶ በላይ ፈቃዱ ያለፉት 3 ወራት የፓርቲው ፕሬዘዳንት ሆነው ማገልገላቸው አይዘነጋም፡፡