-የሰልፉን ቅስቀሳ ተከትሎ የፓርቲው ወጣት አመራሮች ታስረዋል
.አንድነት ፓርቲ የጠራው የነገው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ተጠናክሮ ቀጥሏል
አንድነት ፓርቲ ለነገ እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በኢህአዴግና በምርጫ ቦርድ በኩል ፓርቲው ወደ ምርጫ ውድድር እንዳይገባ የሚደረገውን እንቅስቃሴና ድርጊት በመቃወም የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ በፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉን ተከትሎ ዛሬ ጥር 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃም፣ ምክትል ኃላፊው አቶ ንዋይ ገበየሁ፣ የኤዲቶሪያል ቦርድ ኃላፊው አቶ ሰለሞን ስዩም እና የፓርቲው የአዲስ አበባ ወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ቸኮል እና ሌሎች አመራሮች አቶ ያሬድ አለማየሁ፣ አቶ ሲሳይ ጌትነት፣ አቶ ማቲያስ ሐረጉ በፀጥታ ይሎች መታሰራቸውና ወዳልታወቀ ስፍራ የተወሰዱ ሲሆን፤ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት አቶ አስራት አብርሃም፣ አቶ ንዋይ ገበየሁ፣ አቶ ሰለሞን ስዩም እና አቶ ስንታየሁ ቸኮል መፈታታቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ፓርቲው ሰልፉን እንዲጠራ ያስገደደው ምርጫ ቦርድ ከሀገሪቱ የምርጫ አዋጅ ህግ አግባብ ውጭ በአንድ ወር ውስጥ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በመወሰኑ ሲሆን፤ ቅሬታ ነበረን በሚል ጥያቄ ካቀረቡት ዋነኞቹ አቶ አየለ ስሜነህ እና አቶ ኢሳይያስ ቱሉ ምርጫ ቦርድ እና ባልፈለግነው መንገድ ፓርቲውን ለሁለት ለመክፈል በመሞከሩ፣እኛ ደግሞ አንድነት አንድ ነው እንዲከፈልም ስለማንፈልግ ተመልሰን ወደ ዋናው ፓርቲያችን ቢሮ ተመልሰናል ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ከዚህ ቀደም አንድነት ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. በጠራው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እንዲታዘብ ጥሪ ሲደረግለት እነ አቶ አየለ ስሜነህ ሌላ ጠቅላላ ጉባኤ ለማድረግ ደብዳቤ ስላስገቡ ቦርዱ ሁለት ቦታ ለመታዘብ ወኪል መላክ እንደማይችል በጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፓርቲው ደብዳቤ መፃፉ ታውቋል፡፡
አቶ አየለ ስሜነህ በበኩላቸው እኛ ጠቅላላ ጉባኤ አልጠራንም፣ የነበርነው የአንድነት ፓርቲ አባላት ከ15 አንበልጥም፤ ነገር ግን የፓርቲው አባላት ያልሆኑ ከ60 በላይ ሰዎች በስብሰባችን ላይ ተገኝተዋል፣የሆቴል አዳራሽ ኪራይ ማን እንደከፈለ አናውቅም፣ ተከፍሎላችኋል እዛ ሆቴል ሂዱ እንባላለን፣ይሄ ሁሉ ስላላማረን እና ፓርቲያችን አንድነት አንድ ስለሆነ ወደ ፓርቲያችን ተመልሰናል ሲሉ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፓርቲው ጠቅላላ ጉባዔ እንዲታዘብ ለቀረበለት ጥሪ እነ አቶ አየለ ስሜነህም ጠርተውናል ሲል በፃፈው ደብዳቤ ማስታወቁ አይዘነጋም፡፡ አቶ አየለ ስሜነህ በበኩላቸው እኛ ምንም ዓይነት ጠቅላላ ጉባኤ አልጠራንም፣በመካከላችን የነበረው ጥቂት አለመግባባት እንዲፈታ ስንል እንጂ ከፓርቲው ህልውናም ሆነ አሰራር ጋር ቅሬታም ሆነ ጠቅላላ ጉባኤ ይጠራ የሚል ጥያቄ አላቀረብንም ሲሉ አስታውቀዋል፡፡
በአሁን ወቅት ጥያቄ ነበረን ያሉት አቶ አየለ፣ ያለንን ጥያቄ በፓርቲያችን ውስጥ ሆነን እንፈተዋለን፣ ወደ ውጪ ይዘን መውጣታችን ትክክል እንዳልነበረና እኛ ባላሰብናውና ባልፈለግነው መንገድ ፓርቲው ላይ በእኛ ስም አደጋ ለመፍጠር እየተሰራ እንዳለ ስንገዘነብ ተመልሰናል፣ መጀመሪያም ቢሆን ፓርቲው አልተከፈለም፣ እኛም ጥያቄ አቀረብን እንጂ ከፓርቲው አልወጣንም ሲሉ አክለዋል፡፡ አቶ አየለ ስሜነህ ለጋዜጠኞች የሰጡትን መግለጫ ለራሱ ለምርጫ ቦርድ ግልባጭ ማድረጋቸውንም አስታውቀዋል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ጥያቄ አቅርበው የነበሩት አቶ አየለ ስሜነህ ወደ ፓርቲው መመለሳቸውን ቢያሳውቁም፤ ምርጫ ቦርድ ግን በነ አቶ አየለ ስሜነህ ስም ሌላ አካል እያደራጀ መሆኑን በመጥቀስ ፓርቲው ድርጊቱን ለማውገዝ የሰልፍ መጥራቱን ይፋ አድርጓል፡፡ ፓርቲው ድርጊቱን የኢትዮጵያ ህዝብም እንዲረዳውና እንዲያወግዘው ለነገ እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ኣ.ም. የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉን መጥራቱን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ከዚህ በኋላ ፓርቲው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በመላ ሀገሪቱ ማካሄድና ነውጥ አልባ የነፃነት ትግሉን አጠናክሮ ከመቀጠል ውጭ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማይጠራ ማሳወቁ አይዘነጋም፡፡ ወደ ፓርቲያቸው ስለተመለሱት አቶ አየለ ስሜነህ እስካሁን ባይዘግብም ፓርቲው እንደተከፈለ አድርገው ከሬዲዮ ፋና እና ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በተደጋጋሚ ከሚያቀርቡት በስተቀር ምርጫ ቦርድ እስካሁን የሰጠው ምላሽ የለም፡፡
የነገው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መነሻ አዲስ አበባ ቀበና መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ፊትለፊት ከሚገኘው የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት ሲሆን፤ የሰላማዊ ሰልፉ መነሻ ሰዓት ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት መሆኑንም ታውቋል፡፡
የሰልፉ መዳረሻ ቦታ አዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ጀርባ እና ዋናው ፖስታ ቤት ፊትለፊት በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ መሆኑን ፓርቲው አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት (እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም.) የተቃውሞ ሰልፉ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በደብረ ማርቆስ፣ በአርባምንጭ አካባቢ ከምባ ወረዳ፣በጂንካ እና በሸዋ ሮቢት እንደሚደረግ በፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት በመወሰኑ በክልሎችም የሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ቀጥሏል፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ቀኑ እንዲራዘም የመንግስት አካላትና ዲፕሎማቶች ጥረት ቢያደርጉም፤የአንድነት ፓርቲ ምክር ቤት ዛሬ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ መብታችንን ከእንግዲህ ለምነን አናገኝም፣ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉም በታቀደለት መሰረት ይቀጥል ሲል መወሰኑን ፓርቲው አስታውቋል፡፡
ፓርቲው ከላይ ከተጠቀሱት 5 ከተሞች በተጨማሪ በተከታታይ በሌሎች የሀገሪቱ ከተሞችም የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉ እንደሚቀጥል ይፋ አድርጓል፡፡