ሁለት ታዋቂ የአውሮፓ ኩባንያዎች በኦሞ ሸለቆ ጥጥ የተሠሩ ምርቶች አንገዛም አሉ

ዮሐንስ አንበርብር

 ታዋቂዎቹ የአውሮፓ ጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎች የጀርመኑ ቼቦና የስዊድኑ ኤችኤንድኤም በኢትዮጵያ ኦሞ ሸለቆ ውስጥ የተመረተ የጥጥ ምርትን የሚጠቀም የጨርቃ ጨርቅ ምርቶች እንደማይገዙ መግለጻቸው ተሰማ፡፡

omo1

 የኢትዮጵያን የልማት እንቅስቃሴ ለመገደብና ጥላሸት ለመቀባት የሚደረግ የሰብዓዊ መብት አቀንቃኞች ዘመቻ መሆኑን፣ የኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ልማት ኢንስቲትዩት በመግለጽ አጣጥሎታል፡፡

ሁለቱ ታዋቂ የጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎች በበርካታ የዓለም አገሮች ሰፊ ቅርንጫፍ መደብሮች እንዳሏቸው የሚታወቅ ሲሆን፣ በኦሞ ሸለቆ ከሚመረት ጥጥ ጋር ግንኙነት እንደሌላቸው ማሳወቅ የጀመሩት ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የምዕራብ የሰብዓዊ መብት አቀንቃኝ ተቋማት የኦሞ ሸለቆ ነዋሪዎች ከመሬታቸው በመንግሥት እንዲፈናቀሉ ተደርገው መሬቱ ለጥጥ ምርት መዋሉ፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ነው በሚል ባናፈሱት መረጃ ነው፡፡ ሁለቱ ታዋቂ ኩባንያዎች ደግሞ የሰው ልጆችን ሰብዓዊ መብትና የአካባቢ ጥበቃ እንደሚያስከብሩ የሚያሳውቁ በመሆናቸው ነው፡፡

ኩባንያዎቹ ከሁለት ዓመት በፊት ቢሯቸውን በአዲስ አበባ ከፍተው በኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎች የተመረቱ ጨርቆችን በጥሩ ዋጋ መግዛት መጀመራቸው ይታወሳል፡፡ በመጀመርያ የጀርመኑ ኩባንያ ቼቦ ነው በኦሞ ሸለቆ የሚመረት የጥጥ ምርቶች መቀበል ማቆሙን የገለጸው፡፡ በዚህ ሳምንት ኤኮ ቴክስታይል በተባለው ድረ ገጽ በጉዳዩ ላይ መረጃ የሰጠው ኤችኤንድኤም መሬት መቀራመትን (ላንድ ግራቢንግ) እንደ ሰብዓዊ መብት ጥሰት ስለሚወስድ እንደሚቃወም ገልጿል፡፡ ድርጊቱ በተጨማሪም የተባበሩት መንግሥታትን የሰብዓዊ መብት መርህና የኤችኤንድኤም ድርጅትን የሰብዓዊ መብት ፖሊሲ እንደሚጥስ አክሏል፡፡ በመሆኑም በዋናነት የጨርቃ ጨርቅ ምርት ለሚያቀርብለት የቱርኩ አይካ አዲስ በዚህ አካባቢ የተመረተ ጥጥ ተጠቅሞ የሚያመርተውን ጨርቅ እንዳያቀርብለት ማሳወቁን ገልጿል፡፡

Cotton field near Weita. Omo Valley. Ethiopia.

የኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ልማት ኢንስቲትዩት ጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎችንና ልማቱን የሚደግፍ፣ ገበያና አዲስ ቴክኖሎጂዎችን ወደ አገር የሚያቀርብ የመንግሥት ተቋም ነው፡፡ የተቋሙ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ባንተይሁን ገሠሠ በጉዳዩ ላይ ተጠይቀው፣ የዚህ ዓይነቱ ዘመቻ የሰብዓዊ መብት አቀንቃኝ ነን ባዮች ተግባር መሆኑን ጠቅሰው፣ የጥጥ ልማት በሚከናወንበት አካባቢ መንግሥት እንኳን ሰው ሊያፈናቅል ቀርቶ እያሰባሰበ የልማት ተጠቃሚ እያደረገ ነው ብለዋል፡፡

በአካባቢው በጣም ጥቂት አርብቶ አደሮች ብቻ የሚኖሩበት ለእርሻ የሚመች በጣም ግዙፍ መሬት መኖሩን የጠቀሱት ኃላፊው፣ ‹‹አርብቶ አደሮቹ ሳር ካለ በአካባቢው ይቆያሉ፡፡ ከሌለ አካባቢውን ለቀው ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ከዚህ ውጪ ሰው ያልሠፈረበት አካባቢ ነው፤›› ብለዋል፡፡ አርብቶ አደሮቹ በአካባቢው ረግተው እንዲቆዩና ቋሚ የእርሻ መሬት ማረስ እንዲለምዱ መንግሥት እያስተባበረ እንደሚገኝና በአሁኑ ወቅትም 80 ሔክታር መሬት ላይ አርብቶ አደሮቹን በማስለመድ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ለጥጥ እርሻ የተዘጋጀ 116,859 ሔክታር መሬት በአካባቢው በአሁኑ ወቅት መኖሩንና ከዚህ ውስጥ የለማው 70,867 ሔክታር ብቻ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በአካባቢው ጥጥ በማምረት ላይ የሚገኙ 22 ኩባንያዎች መኖራቸውንና በአሁኑ ወቅት ከተዘጋጀው 116 ሺሕ ሔክታር መሬት በላይ ማስተናገድ እንደሚችልም ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የሰብዓዊ መብት አቀንቃኞቹን ዘመቻ መንግሥትም፣ እኛም፣ ኤችኤንድኤምና ቼቦም ያውቁታል፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ አሁንም እነዚህ ኩባንያዎች ከኢትዮጵያ እየገዙ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ጉዳዩን በተመለከተ የአይካ አዲስ የሥራ ኃላፊዎች ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ጨምሮ ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: