ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ሳሪስ አካባቢ በሚገኘው ፍሬህይወት አጠቃላይ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አጠገብ ከባቡር መንገድ ስራ ጋር በተያያዘ በተደረገ ቁፋሮ የትምህርት ቤቱ አጥር ተደርምሶ 11 ተማሪዎች ላይ ጉዳት አድርሶ የነበረ ሲሆን፤ ከተጎዱት መካከል ተማሪ ፅዮን ንጉሴ ሆስፒታል ውስጥ የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላት በደረሰባት ከባድ ጉዳት ምክንያት ህይወቷ ማለፉ ተሰምቷል፡፡ የተማሪ ፅዮን ንጉሴ የቀብር ስነስርዓትም ዛሬ ሳሪስ አካባቢ በሚገኘው ብሔረ ፅጌ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን መፈፀሙን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡
የትምህርት ቤቱ አጥር የተደረመሰው ቻይናዎች ጥንቃቄ በጎደለው መልኩ አጥሩ ጥግ ቁፋሮ በሚያደርጉበት ወቅት ተማሪዎች ዕረፍት ላይ ስለነበሩ አንዳንዶቹ ሲጫወቱ ሌሎች ደግሞ በአጥሩ ጥቅ ሲያጠኑ አደጋው መድረሱን በወቅቱ የነበሩ የዓይን እማኞች ተናግራዋል፡፡ በወቅቱ በቻይናዎቹ ድርጊት የተበሳጩ ተማሪዎቹ ቁጣቸውን ሲገልፁ በስፍራው በነበሩ ቻይናዎችና የአዲስ አበባ ፖሊሶች በርካታ ተማሪዎች መደብደባቸውም ተጠቁሟል፡፡ ስለተፈጠረው አደጋም ሆነ ስለተማሪዎቹ ጉዳት የመንግስት አካላት እስካሁን ምንም ያሉት ነገር የለም፡፡