ባለፉት 9 ወራት በፖሊስ ቁትጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የነበሩት 6 የዞን 9 ጦማርያንና 3 ጋዜጠኞች ላይ አቃቤ ህግ በዛሬው ዕለት ጥር 20 ቀን 2007 ዓ.ም. አሻሽዬ አቅርቤዋለሁ ያለውን የክስ ቻርጅ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ የወንጀል ችሎት ተቀባይ አድርጎታል፡፡
በዚህም መሰረት ተከሳሾቹ በአሸባሪነት ወንጀል እንደሚጠየቁና ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡ ዛሬ ጠዋት በነበረው የክስ ሂደት ወቅት ጠይቋቸው ጉዳዩን ለከሰዓት አስተላልፎት ነበር፡፡ ነገር ግን ከጥቂት ሰዓታት በፊት በነበረው የክስ ሂደት ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን ለ17ኛ ጊዜ ለሚቀጥለው ማክሰኞ ጥር 26 ቀን ቀጠሮ በመስጠት ተበትኗል፡፡
ስድስቱ የዞን 9 ጦማርያንና ሦስቱ ጋዜጠኞች ከባለፈው ዓመት ሚያዚያ 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የከረመ ቢሆንም የክስ ሂደቱ ላይ ግን በርከት ያሉ የህግ ሂደትን ያልተከተሉ ሁኔታዎች ሲስተዋሉ መቆየቱን አዲስ ስታንዳርድ ዘግቧል፡፡