አዲስ አበባ ቀበና የሚገኘው የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዋና ጽህፈት ቤት በፖሊስ እና ደህንነቶች ቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት በቁጥጥር ስራ የዋለው ምርቻ ቦርድ ለእኔ ይታዘዘኛል በሚል የፓርቲውን ስምና ህልውና ለነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ማስረከቡን ተከትሎ ነው፡፡ ፖሊስ አርብ ጥር 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ጽህፈት ቤቱን ከመቆጣጠሩ በፊት የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ስብሰባ ተቀምጠው እንደነበርና በዕለቱ ከሰዓት በኋላ የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት በምርጫ ቦርድ ውሳኔ ጉዳይ ለመምከር ወደ ጽህፈት ቤቱ ሲያመሩ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተረጋግጣል፡፡ በዕለቱ ጠዋት ስራ አስፈፃሚው በጉዳዩ ዙሪያ ከመከረና ከተወያየ በኋላ ለምሳ ወጥተው ለምክር ቤቱ ስብሰባ ሲመለሱ ወደ ቢሮው መግባት የተከለከሉ ሲሆን፤ ቢሮው በፖለስ ቁጥጥር ስር በመዋሉ ቀጠሮ የተያዘለት የፓርቲው ምክር ቤት ስብሰባም ሳይካሄድ መቅረቱ ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ለምሳ ሲወጡ ትተዋቸው የሄዷቸውን ተሸከርካሪም ሆነ ማንኛውንም ወረቀት ይዘው እንዳይወጡ ከታገዱ በኋላ ፖሊሶቹ በስልክ በተሰጣቸው ትዕዛዝ ስራ አስፈፃሚዎቹ መኪናቸው ብቻ ተፈትሾ እንዲወጣ መደረጉን የፓርቲው ምክትል ፕሬዘዳንት አቶ ግርማ ሰይፉ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ተናግረዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን ሲቆጣጠር ከስራ አስፈፃሚው ውጭ በቢሮ ያሉ የፅህፈት ቤት ሰራተኞችና ሌሎች የፓርቲው አባላትና አመራሮች ላልተወሰነ ጊዜ ከቢሮ እንዳይወጡ፣ከግቢ ውጭ የነበሩትም እንዳይገቡ መደረጉን የአይን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን በኃይል ሲቆጣጠር ምንም ዓይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አለመያዙ ታውቋል፡፡ የአንድነት ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት በምርጫ ቦርድ እነ ትዕግስቱ አወሉ ከተመረጡ በኋላ አሁንም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ይገኛል፡፡
በተመሳሳይ ዜና አዲስ አበባ ቸርችል ጎዳና አካባቢ የሚገኘው የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ዋና ጽህፈት ቤትም በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተጠቁሟል፡፡ ፖሊስ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ የፓርቲዎቹን ዋና ጽህፈት ቤት ለምን እንደተቆጣጠረ እስካሁን የተገለፀ ነገር የለም፡፡ የአዲስ ሚዲያ ፖሊስ ምንጮች እንዳረጋገጡት ከሆነ፤ፖሊሶችም የፓርቲዎቹን ቢሮዎች ተቆጣጠሩ የሚል ትዕዛዝ ከመሰጠቱ በስተቀር ለምን እንደተቆጣጠሩ ራሳቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁ ተጠቁሟል፡፡ ምርጫ ቦርድ መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ሂደትን ተክትሎ በዋዜማው ሁለት አንድነት እና መኢአድ ፓርቲዎችን በማፍረስ ሌላ አዲስ ታሪክ አስመዝግቧል፡፡ ቀደም ሲል “የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ከህወሓት/ኢህአዴግ የተሰጠውን ትዕዛዝ ከማስፈፀም ውጭ ነፃና ገለልተኛ አይደለም፣ቦርዱን የሚመሩት ስራ አስፈፃሚዎችም ተቋሙን ለመምራት የሚያስችል አቅምና ቁርጠኝነት ስለሌላቸው ለተቋሙ አይመጥኑም፣..በሚል በተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተደጋጋሚ ትችት ይቀርብበት እንደነበር አይዘነጋም፡፡
አሁን ያለው የቦርዱ እንቅስቃሴ በቀጣይ ቀናትም ከምርጫው ዋዜማ እስከ ድህረ ምርጫ አዳዲስ ውሳኔዎችን እና እንቅስቃሴዎችን ሊያሳይ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡