በአብዛኛዎቻችን ኢትዮጵያዉያን አንድ ጥሩ ባህል አለን፡፡የምንወደዉንና የሚመቻንን ሰዉ በሞት ስናጣ እርም የማዉጣት ባህል፤ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሆኖ አገኘሁት፡፡ሠዉና የፖለቲካ ድርጅ ባይገናኙም በጉልበተኛ ሃይል እንዲገናኙ ሲደረግ ከማገናኘት ዉጪ ምርጫ የለንምና እናገናኛቸዋልን፡፡
አቅምና ሁኔታዎች በፈቀዱት መጠን የወቅቱን ያገራችን ችግር በመፍታት በኩል የራሱን አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት፤ የኢህአዴግ ሰዎችን ጨምሮ ያብዛኛዉ ተራማጅ ኢትዮጵያዊ ቤት እንዲሆን አድርገን ስንገነባዉ(ሲፈጥሩትም ለዚህ ኣላማ ነበር ተብሎ ይታመናል) የነበረዉን አንድነት ፓርቲን በፖለቲካዊ ዉሳኔ የሆነዉ እንዲደርስበት ተደርጓል፡፡አማራጭ እንዲኖር የማይፈልጉት በከፍተኛ የመንግስት ሃላፊነት የተመደቡቱ ጥቂት የህወሓት ቡድኖች የማይጠቅማቸዉን ዉሳኔ እንደወሰኑ ይታወቃል፡፡ ተዉኔቱ በማን ተዘጋጅቶ እነማን እንደተጫወቱትና እነማን ደግሞ ለህዝቡ እንዳደረሱት በተደጋጋሚ ገልጸነዋል፡፡
ፓርቲዉን በተለያዩ ስሞች ሲከሱና ሲፈርጁ ቆይተዉ አመራሩንም በእስርና ድብደባ እያሹ እንዳልተንበረከከና ይበልጥ መጠናከሩን ሲያረጋግጡ ለዚህ ዉሳኔ በቅተዋል፡፡ በ40 ዓመታት ታሪኩ ፓርቲዎችን በመብላትና ከዉስጥና ከዉጭ የሚነሳ ልዩነትን በማቻቻል ሳይሆን በማጥፋት የሚታቀወቀዉ ጥቂት የህወሓት ቡድን አንድነት ፓርቲን ከማጥፋት አሁን ወደ መረጠዉ ደረጃ እንዲወርድ አድርጓል፡፡ታሪክ ሁሉን ይፈርዳል፡፡በጨለማዉ ዘመን ግፍ የተፈፀሞባቸዉ ቡድኖችና የፈሰሰዉ ደምም ተደብቆ ኣልቀረም፡፡ፖለቲካችንን ለማዘመንና ያለፈዉ ግፍ ሁሉ ባይረሳም በይቅር መታለፍ አለበት ብለን ለተነሳን ሃይሎችም እድሉን (በጉልበት በህዝብ ሃብትና በያዙት ስልጣን ተጠቅመዉ) ዘግተዉብናል፡፡ በደም መጨማለቅ በዚህ ያበቃ ዘንድ አሁንም እንታገላለን፡፡የፖለቲካ ትግሉ ሂደትም አይቆምም፡፡ያዉም ይብልጥ የመጠናከር እድል አግኝቷል ተብሎ ይታመናል፡፡የሚያቆመዉ ሃይል የለም፤መጪዉ ግዜ የለዉጥ ነዉ፡፡ለዉጡ እንደይሰረቅና ለሁሉም ይመች ዘንድ የጋራ ትስስርን እንደሚጠይቅ እሙን ነዉ፡፡
ለግዜዉ ከጀርባ ያለዉን ፖለቲካዊ ግፊት ለሌላ ፖለቲካዊ ትግል ትተን የምርጫ ቦርድ ዉሳኔን በመቃወም ክስ መስርተን ወደ ፍርድ ቤት ተብየዉ ወስደንዋል፡፡ ወደ ህግ ለመዉሰድ ስንወስን የፓርቲ ስምና አርማ አስጨንቆን አይደለም፡፡ የደጋፊዎችና አባላት ንብረት ለይምሰልም ቢሆን ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ ፖለቲካዊ ዉሳኔ እንግበዉ በመጡ ከህዝብ ግብር በተሰበሰበ ደሞዝ የሚተዳደሩ የክፍለ ከተማ ፖሊስ ሃይሎች ( ህዝባዊ ሃለፊነትን የተሸከመ ተቋም በፖለቲካ እዝና ዉሳኔ የፓርቲን ንብረት ይዘርፋል የሚል እምነት አልነበረንም) ስለተዘረፈብን ሃላፊነታችንን ለመወጣትና ታሪካዊ እልባት እንዲኖረዉ ለማስቻል ነዉ፡፡እንጂማ ራእያችን በእያነዳንዳችን ዉስጥ ቢሆንም የወቅቱ ትግል ግን የነፃነት መሆኑን አጥተነዉ አይደለም፡፡
በወቅቱ የብሔራዊ ስራ አስፈፃሚዉ የወሰነዉ ዉሰኔ የመድብለ ፓርቲ ስርኣቱ ከምን ግዜዉም በላይ ፈተና ላይ መዉደቁና አዲስ ፓርቲ መመስረት ችኮላና ህዝቡን ስርአቱ ለመድብለ ፓርቲ አሁንም ይመቻል፤ጥፋቱ የኛ ነዉ ብሎ መዋሸት መሆኑ፤እስኪያጠፋቸዉ ድረስ ሌሎች ፓርቲዎች ጋ መቀላቀል በተላይም ከምርጫዉ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ተስፋ ያላቸዉ አባላት የግል ምርጫቸዉ መሆኑንና አመራሩም ይህን እንደማይቃወም፤የፓርቲዉ አባላት ጉዳዩ በፍ/ቤት እስኪቋጭ ድረስ አመራሩን እንዲጠብቁ ይሀም ለብሔራዊ ምክር ቤቱ ከሰዓት እንዲቀርብና ተወያይቶ ዉሰኔ እንዲሰጥበት የተስማማ ሲሆን በወቅቱ ሁለት አባላት ብቻ አልተገኙም፡፡ከሰኣት ቢሮዉ የፖሊስ ደንብ በለበሱ የመንግስት አካላት ተዘረፈ፡፡ይህ ደግሞ አእላፍ ወንድሞቻችን ላለፉት 40-50 አመታት በተለያየ ጉራ ተሰልፈዉ በተሰዉለት በተላይም በትግረዋይ ደም/ የትግል ዉጢት ሌላዉ ቀልድ እንደመሆኑ ጉዳዩ አብዛሃዉ የአንድነት ደጋፊና አባል በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንወስደዋለን ባልነዉ መሰረትእየታየ ይገኛል፡፡በመሆኑም ጉዳዩን መከታተል የእያነዳንዱ የአንድነት አባልና ደጋፊ የህሊና እዳ ይመስለኛል፡፡በአንድነት ቀብር ላይ አሁንም አንድነታችንን በማረጋገጥ ባብዛሃ ዉሳኔ ቀጣዩን መንድ መጓዝ እንጂ ልንለያይ የሚጋብዝን መንገድ መከተል ያለብን አይምስለኝም፡፡ካለፉት የተቃዉሞ ጎራ በጎዉን ትምህርት መቅሰም የሚኖርብን እንዳለ ይሰማኛል፡፡በችኮላ ፓርቲ ለመመስረት የሚደረግ ሩጫ የስልጣን ሀይልነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ለህዝባችን ፋይዳ አለዉ ብየ አልገምትም፡፡ ምርጫቸዉ ላደረጉት ጓዶቼ ግን ስህተት ቢሆን ምርጫቸዉን አከብራለሁ፡፡
ጉዳያችንን ወደ ፍርድ ቤት ስንወስደዉ በፍትህ ተቋማቱ ምናልባትም በሰላማዊ ትግል ስልት ስርኣቱን ለመለወጥ ከሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች መካከል ከቀድሞዉ ቅንጅት ቀጥሎ የግፍ ፍርድ ሲበየንበት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት እንደሆነ ስተነዉም አይደለም፡፡ ዱባና ቅል አበቃቀሉ ለየቅል የሚለዉ ብሂል እንዳለ ሆኖ ብርቱኳን መደቅሳ፤ዳኛ ፍረህይወት እና ሌሎች (ለህሊናቸዉ የተገዙ ዳኞች አልፎ አልፎም ቢሆን) የተገኙት በዚህ አፋኝ ስርኣት በዘረጋዉ መዋቅርና በህዝባችን ዘንድ እምነት በታጣባቸዉት የፍትህ ተቀዋማት ውስጥ ነዉ፡፡ታድያ እየተፈተኑ የሚወድቁትን ተቋማት ሳይሆን ግለሰብ ዳኞችንም ለመፈተን ይህን ታሪካዊ ክስ ስናቀርብ የግለሰቦችን የህሊና ዳኝነትንም ተስፋ ባለመቁረጥ ጭምር ይሆናል፡፡ ሁሌም እንደምንለዉ ፓርላማ ተቀምጦ የተከበሩ እየተባሉ ለመጠራት ሳይሆን ትግላችን ለለዉጥ ነዉና ድንክየዉን አንድነት ቢመለሱልንም ባይመሉሱልንም፤ የህዝብ ከሆነዉ ትግል መሃል ሆነን ፖለቲካዉን ከመስራት አንታቀብም፡፡ዉሳኔዉም በሁሉም የለዉጥ ሃይሎች ቀጣይ እንቅስቃሴ የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡የአንድነት ልጆች ህወሓት ለመደዉ የጥባጥቤ ጨዋታዉ ቦታ ይኖረናል ተብሎ አይታሰብም፡፡አንድነታቸንን እንደ ጠበቅን የሚቀብሩት ከሆነ የአንድነት ፓርቲ “ቀብር” ላይ እንገናኝ፤ መቃብሩ ላይም እርም እናዉጣና የአንድነት ሃይሎች ዳብረን እንወጣ ዘንድ ትግሉ ግድ ይለናል!
ላለፉት አምስት አመታት ብዙዎቹ በእስር የሚማቅቁበት የተሰደዱለትና የቆሰሉ፤ የደሙለት ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የብዙ ወገኖችን እና ተቋማትን የፍትህ ጥያቄ በማዉሳት ባደባባይ የጮኸዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡በኢትዮጵያዊነት ማእቀፍ ዉስጥ የብሄረሰቦችን እና የቡድኖችን መሰረታዊ የፖለቲካ ጥያቄ ለመመለስ ቁርጠኝነት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ የህዝብን ጥያቄዎች በጠራ መልኩ በማዉሳት ድምጻቸዉን ከሚያሰሙ ፓርቲዎች ዉስጥ ተጠቃሹ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የቅርርብ፤የመደማመጥና የመከባበር ፖለቲካ እንዲኖር ባሳለፋቸዉ አጭር አመታት ጥረት ያደረገ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ በዚህም ከህዝብ ብቻ ሳይሆን ለሃገራቸዉ በጎዉን ለዉጥ የሚሹ በርካታ የኢህኣዴግ ተራ አባላትና አንድንድ ባለስልጣናትም ጭምር በበጎ አይን ይመለከቱት እንደነበር ገምግመናል፡፡ በዚህ ወቅት አወንታዊ ተፅእኖ ያመጣል ተብሎ በመፈራቱ ግን ከ40 አመት በኃላም ትቂቱ የህወሓት ቡድን በለመደዉ ስልቱ በልቶታል፡፡
ይህን ድርጊት ለዉጥ ፈላጊ ሃይሎች በጥሞና ይከታተሉታል ተብሎ ይገመታል፡፡የምትችሉ ሁሉ ፍርድ ቤት በመገኘት እስከ ታሪካዊዉ ዉሳኔ እለት ድረስ ሂደቱን ለመዘገብና ለታሪክ ምስክር ለመሆን፤ እንዲሁም አጋርነታችሁን ለመግለፅ ትገኙ ዘንድ የክብር ጥሪ ተላልፏል፡፡እዉነተኛ አንድነት ነባር አመራር፤አባለትና ደጋፊዎች ጉዳዩን በአንድነት እንቋጭኛ እንደስማቸን በአንድነት ቦይ እንፈስ ዘንድ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡
አቶ ተክሌ በቀለ (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)