ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በሜዴትራኒያን ባህር ከሊቢያ ወደ አውሮፓ በስደት ሲጓዙ ከነበሩ 700 ሰዎች መካከል በርካቶች መሞታቸውንና የ28 ሰው ህይወት ብቻ በጣሊያን ባህር ኃይሎች ማትረፍ ቢቻልም፤ የአብዛኛው ተጓዥ ሕይወት ማለፉ ታውቋል፡፡ ህይወታቸው ካለፉት ውስጥ በርካታ ኤርትራውያን እንዳሉበት ቀደም ሲል የተገለፀ ቢሆንም፤ አሁን እየወጡ ባሉ መረጃዎች በተለይም ከሞት በተረፉ ኢትዮጵያውያን እንደተገለፀ ከሆነ ከ16 በላይ ኢትዮጵያውውን መሞተታቸው ታውቋል፡፡ በጉዞ ጀልባዋ ላይ በደረሰ የመስጠም አደጋ ህይወታቸው ካለፉት መካከል 8 ወጣቶች ከአዲስ አበባ መርካቶ ልዩ ስሙ አባኮራን በሚባል አካባቢ፣ 8 ወጣቶች ከባሌ እንዲሁም የድሬዳዋ ልጆች ህይወታቸው ማለፉን ቢቢኤን እና ፍትህ ሬዲዮን ጨምሮ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ከሀገር ቤት ቤሰቦቻቸውን ዋቢ በማድረግ ያሰራጩት ዘገባ አመልክቷል፡፡
በተለይ ከአዲስ አበባ መርካቶ አባኮራን አካባቢ በጋራ ከተጓዙ 10 ወጣቶች መካከል 9ኙ በአደጋው ህይወታቸው ማለፉን እና አንዱ ከአደጋው የተረፈው ኢትዮጵያዊ ወጣት ጣሊያን እንደገባ ሀገር ቤት ደውሎ ማርዳቱ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም መሰረት የ8ቱ ቤተሰቦች ሀዘን ሲቀመጡ የአንዱ ወጣት ወላጆች ግን እስካሁን የልጃቸው ህይወት አልፏል መባሉን እንዳላመኑ እና እንዳልተቀበሉም የአካባቢው ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ በሚያዝያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በሊቢያ ሜዲትራኒያን ባህር በደረሰው አደጋ ህይወታቸው ካለፈ የአዲስ አበባ አባኮራን ሰፈር ወጣቶች መካከል አብዱ ጅላል ወጉ (ሙራድ)፣የሐዋሳ ዩኒቨርስቲ ተማሪ የነበረው ኑሩ መሐመድ፣አብዱልከሪም ዘይኒ፣ ሰይድ ይመር፣ አሊ መሐመድ፣ ነጃ ሳቢር አወል እና የኢንፎኔት ኮሌጅ ተመራቂ የነበረው ኢድሪስ አደም እና ወጣት ሸበቴ ህይወታቸው በማለፉ ቤተሰቦቻቸው ተረድተው ሀዘን መቀመጣቸው ተጠቁሟል፡፡ በሰጠመችው ጀልባ ከባሌ አካባቢ ህይወታቸው ካለፉት ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል አብዱረዛቅ አቡበክር፣ በሪሲና አብዱልወሃብ፣ ሰይፈዲን አሊዪ፣ ሬድዋን ሙሃመድ፣ አሊይ ረሻድ፣ ኢሳ አማን፣ ኑእማን ሁሴን እና ሲራጅ ሙሃመድ እንደሚገኙበት ተጠቁሟል፡፡ በዚህ አደጋ ከድሬዳዋ አካባቢም ህይወታቸው ያለፈ ወጣቶች እንደሚገኙበትና ቤተሰብም ተረድቶ ሀዘን መቀመጣቸውን የቢቢኤን ዘገባ አመልክቷል፡፡
በዚህ አደጋ ከኢትዮጵያውያን በተጨማሪ ከ350 ያላነሱ ኤርትራውያንን ጨምሮ በርካታ የሶማሊያ እና የተለያዩ የአፍሪካ ሀገር ዜጎች ህይወታቸው ማለፉን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ ባለፈውበደደቡብ አፍሪካ፣ በየመን እንዲሁም በሊቢያ በረሃ በዓለም አቀፉ አሸባሪው አይ ኤስ አይ ኤል 28 ኢትዮጵያውያን መገደላቸው ተከትሎ በመላ ሀገሪቱ ያለው የሀዘን ድባብ ሳያባራ አሁን ደግሞ በሊቢያ ሜዴትራኒያን ባህር ሰጥመው መሞታቸው ህዝቡን የበለጠ ሀዘን ውስጥ መክተቱ ታውቋል፡፡
ባለፈው ሚያዝያ መጨረሻ 2007 ዓ.ም. በሊቢያ ታስረው የነበሩ 27 ኢትዮጵያውያን በግብፅ መንግሥት ጥረት እንዲለቀቁ ተደርገው ወደ ካይሮ ሲገቡ የግብፁ ፕሬዘዳንት አብዱል ፈታህ ኤል ሲሲ በአውሮፕላን ማረፊያው ድረስ በመሄድ አቀባበል ማድረጋቸው አይዘነጋም፡፡