ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ የአዲስ አበባ ወጣቶች አመራር የነበረውና በአሁን ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ አባል ወጣት ስንታየሁ ቸኮል 6 ወር እስራት ተፈረደበት፡፡ ወጣት ስንታየሁ ቄራ አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ሲቪል በለበሱ ደህንነቶች ተወስዶ ከታሰረ በኋላ የፌደራሉ ፍርድ ቤት ቄራ ምድብ ችሎት ቀርቦ የአካባቢው የኢህአዴግ ካድሬዎች ከመሰከሩበት በኋላ እንደተፈረደበት ታውቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ለቀረበበት ክስ መከላከያ ምስክር አሊያም የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርብ ቢጠይቀውም፤ ወጣት ስንታየሁ “ከሳሼም፣መስካሪየም፣ፈራጁም ኢህአዴግ ስለሆነ የመከላከያ ምስክር ብዬ ሰዎችን አላንገላታም፣የቅጣት ማቅለያም አላቀርም፤የፈለጋችሁትን ፍረዱ” ሲል ችሎት ላይ መናገሩ ትውቋል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ በችሎት የተናገርውና የቀረበበት ክስ ከዓመት በላይ የሚያስቀጣ ቢሆንም፤ ፍርድ ቤቱ በ6 ወር እስራት እንዲቀጣ መፍረዱ ታውቋል፡፡
ስንታየሁ ቸኮል ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ሲሆን፤ ከዚህ ቀደም ከቀድሞው አንድነት ፓርቲ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ የፀጥና ደህንነት ኃይሎች ተደጋጋሚ ሲታሰርና ሲደበደብ እንደነበር ይታወቃል፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ በተደረጉ በተለያዩ የስርዓቱ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ላይ የስርዓቱን ድርጊት የሚያመለክቱ ልዩ መፈክሮችን ይዞ በመውጣትም ይታወቃል፡፡
በተያያዘ ዜና ሰኞ ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ኦዲትና ኢንስፔክሽን ፀሐፊ የነበረው ፋንቱ ዳኜ ሳሪስ አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ሲቪል በለበሱ የፀጥታ ኃይሎች ተይዞ መታሰሩ ታውቋል፡፡ አቶ ፋንቱ በወቅቱ ሳሪስ ፖሊስ ጣቢያ ቢወሰድም እስካሁን ለምን እንደተያዘ እና እንደታሰረ የተገለፀ ነገር እንደሌለ ለማወቅ ተችሏል፡፡ወጣት ፋንቱ ከቀድሞ የአንድነት ፓርቲ ጠንካራ ወጣት አመራሮች መካከል አንዱ እንደነበር ምንጮች አስታውቀዋል፡፡