ከ35 ወራት የፍርድ ሂደት ቆይታ በኋላ ዛሬ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ የወንጀል ችሎት በእስር ላይ ባሉት የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሜቴ አባላት በሆኑት በእነ አቡበክር አህመድ የክስ መዝገብ የአቃቤ ህግን እና የመከላከያ ምስክሮችን ቃል በንባብ አሰምቶ ማጠናቀቁን ተከትሎ ዛሬ በ18 ተከሳሾች ላይ ፍርድ ሰጥቷል።
ከ1ኛ እስከ 9ኛ ያሉት ተከሳሾች በተከሰሱባቸው በፀረ ሽብር ህጉ አንቀፅ አራት ላይ በተዘረዘሩት መቀስቀስ፣ ማነሳሳት እና ማሴር በሚሉ ወንጀሎች ጥፋተኛ ተብለዋል።
ቀሪዎቹ ተከሳሾች በፀረ ሽብር ህጉ አንቀፅ አራት ላይ በተጠቀሰው በመሳተፍ ወንጀል ጥፋተኛ ተብለዋል።
ፍርድ ቤቱ በተከሳሾቹ ላይ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ለሀምሌ 27 ቀን 2007 ዓመተ ምህረት ቀጠሮ ሰጥቷል።
ተከሳሾቹ እና አቃቤ ህግ ከሀምሌ 27 ቀደም ብለውም የቅጣት ማቅለያ እና ማክበጃ አስተያየታቸውን እንዲያቀርቡም አዟል።
ፍርድ ቤቱ ዛሬ ጠዋት ከከሳሽና ከተከሳሽ በኩል በተካሄዱ ክርክሮች አምስት ጭብጦችን መመርመሩ ነው የተመለከተው።
ከአምስቱ ጭብጦች መካከል መንግስት በእስልምና ሃይማኖት ጣልቃ ገብቷል አልገባም? የሃይማኖቱ ተከሳሾችን ከፋፍሏል አልከፋፈለም? እና የመጅሊሱ ምርጫ ከህገ መንግስቱ ጋር ተጋጭቷል? አልተጋጨም? የሚሉት ተጠቃሾች ናቸው።
ችሎቱ እነዚህን ጭብጦች ሲመረምር በተለያዩ ሃገራት ከሃይማኖት ጋር በተያያዘ የሚራመዱ አሰራሮችን ማየቱን በችሎት መግለፁ ተጠቁሟል፡፡
ከዚህ ሰፊ ሃተታ በኋላ መንግስት በሃይማኖት ጣልቃ አለመግባቱን፣ ተከታዮችን አለመከፋፈሉንና የመጅሊሱ ምርጫ ከህገ መንግስቱ ጋር ሳይቃረን በሃይማኖታዊ ስርአት መካሄዱን ከምስክሮችና ከማስረጃ ቃል በማገናዘብ አረጋግጫለሁ ማለቱን ተከትሎ ነው ከሰዓት በኋላ ፍርድ መስጠቱን ኤቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡