ሚኒስትሩ ስለ አንዳርጋቸው ጽጌ በተናገሩት ላይ ጥርጣሬ አለኝ!

ብስራት ወልደሚካኤል

ትናንት ረቡዕ ሐምሌ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት የአማርኛው ፕሮግራም ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ስለ አንዳርጋቸው ጽጌ በተናገሩት ላይ ጥርጣሬ አለኝ፡፡ ጥርጣሬም የመኘጨው ከኢህአዴግ ባህርይ እና ሴራ በመነሳት ሲሆን፤ይህም አስቂኝ እና ምናልባትም እጅግ አጠራጣሪ እና ሊሆን የማይችል ንግግር ሚኒስትሩ በመናገራቸው ነው፡፡ ጥርጣሬየንም እንደሚከተለው አቀርባለሁ፡፡

አንዳርጋቸው ጽጌ

አንዳርጋቸው ጽጌ

1ኛ. የግንቦት 7 ዋና ፀሐፊ የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው ሰኔ 2006 ዓ.ም. በየመን የፀጥታ ኃይሎች ትብብር ታፍነው ለህወሓት መንግሥት ተላልፈው ከተሰጡ ጀምሮ በኢትዮጵያ እስር ቤት ከመገኘታቸው ውጭ የት እንደታሰሩ፣ በምን ዓይነት ሁኔታ ላይ እንዳሉ….እንዳይታወቅና ማንም ቤተሰብ እንዳይጎበኛቸው ተደርጓል፡፡ በብዙ ዲፕሎማሲያዊ ጫና በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ አምባሳደር ግሪጎሪ ዶሪ ብቻ ሁለት ጊዜ እንደጎበኟቸው ይታወቃል፡፡ ይሄንንም በተመለከተ አምባሳደሩ ስለ አቶ አንዳርጋቸው ደህንነት ሁኔታ ስጋት እንዳደረባቸው መናገራቸው አይዘነጋም፡፡
ነገር ግን ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም በቤተሰብም፣ በወዳጅ ዘመድም ሆነ በኃይማኖት አባት እንዳይጎበኙ የተከለከሉትን እና እስካሁንም የትኛው ወህኒ ቤት እንዳሉ ያልታወቁትን አቶ አንዳርጋቸውን የሀገሪቱን ልማት በተለይም ከአዲስ አበባ አዳማ ያለውን እንዲጎበኙ ተደርገው መደነቃቸውን እንዲሁም በሚሰቃዩበት ወህኒ ቤት ላፕ ቶፕ ኮምፒዩተር ተፈቅዶላቸው መፅሐፍ እየፃፉ ወደ መጨረሱ እንደደረሱ ነግረውናል፡፡ ዘይገርም ነው፡፡ ቢሆን ደስ ይላል፤ ግን ሊሆን የማይችልና የማይታመን ነው፡፡

ከህወሓት/ኢህአዴግ ባህርይ አንፃር በቤተሰብ ያውም በወላጆቻቸውና በእህቶቻቸው እና ወንድሞቻቸው እንኳ እንዲጎበኙ ያልተፈቀደላቸው ግለሰብ፤ ላፕ ቶፕ እንዲገባላቸውና መፅሐፍ እንዲፅፉ ሊፈቀድ አይችልም፡፡ ይህ የሚሆን ከሆነ ለምን እነ እስክንድር ነጋ፣ አንዱዓለም አራጌ፣ በቀለ ገርባ (ወህኒ ቤት ሳሉ)፣….ወዘተ በእጅ ፅሑፍ እንኳ የፃፉት ተራ ማስታወሻ እንኳ በየጊዜው እየተበረበረ ሲወሰድ እና ድጋሚም ምንም ዓይነት ነገር እንዳይፅፉ፤ እንደውም ለረጅም ጊዜ ማንኛውም መፅሐፍ እንኳ እንዳይገባላቸው ይከለከሉ እንደነበር እናውቃለን፡፡ በአሁን ሰዓት ራሱ በተለያዩ የሀገሪቱ ወህኒ ቤቶች እንኳን ላፕ ቶፕ ኮምፒዩተር ሊፈቀድ ይቅርና ሊያነቡት የጠየቁት መፅሐፍ እንኳ በማረሚያ ቤቱ አስተዳደር የዕውቀትና አስተሳሰብ ደረጃ ተመዝኖ ካልተፈቀደ እንደማይቻል ይታወቃል፡፡

ታዲያ ለአቶ አንዳርጋቸው ምን ያህል ቢራሩ ነው ላፕ ቶፕ የፈቀዱት? እውነት ከራሩ ለምን በቤተሰብና በአድናቂዎቻቸው እንዲጎበኙ አልተፈቀደም; ከዶ/ሩ እና አመራሮቻቸው መልስ የሚያሻው ጥያቄ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ይህንን ቀላል ጥያቄ የVOA ጋዜጠኛዋ ለሚኒስትሩ ሳታቀርብ እንዴት እንዳለፈችው ገርሞኛል፤ ደንቆኛልም፡፡ ምናልባት የትናንቱ ላይ ተንተርሳ ድጋሚ ተዘጋጅታበት ልታነሳው ካሰበችም እንጠብቃለን፡፡
2ኛ. ከህወሓት/ኢህአዴግ ልምድና ባህርይ አንፃር ሌለው አስገራሚ ነገር፤ አቶ አንዳርጋቸው እየፃፉ ነው የተባለው መፅሐፍ በማን አማካኝነት ከወህኒ ቤት ወጥቶ ለንባብ ሊበቃ ነው? ይሄ ደግሞ ሌላ መልዕክት አለው፡፡

ከዚህ በፊት በስልጣን የቁም እስረኛ የሆኑት ክቡር አቶ አባዱላ ገመዳ ሳይወዱ በግድ ስማቸውን በማዋስ በስማቸው መፅሐፍ መፃፉን ስንቶቻችን እንደምናውቅ አላውቅም፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ ለህወሓት በተለይም ለራሳቸው የስልጣን መደላደል ይሆን ዘንድራሳቸው በመሰላቸውና በሚፈልጉት መንገድ ስለ ኦሮሞ ትግል መፅሐፍ ፃፉ፡፡ ከዚያም በህወሓት ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት መርህ መሰረት አቶ አባዱላ ገመዳ ፈቃዳቸው ሳይጠየቅና የመፅሐፉን ረቂቅ ሳያዩት በስማቸው ለገበያ እንዲበቃ ተደርጎ ራሳቸውም ከአንባቢው እኩል አነበቡት፡፡ በስልጣን የቁም እስረኛም ስለሆኑ ቅሬታም ሆነ አስተያየት መስጠት አልቻሉም፤ በመለስ ዜናዊ ተፅፎ በአባዱላ ገመዳ ስም ግን ገበያ ላይ ውሎ ተነቧል፡፡

አሁን ደግሞ ምንም ዓይነት አካላዊም ሆነ አዕምሯዊ ነፃነት እንዳይኖራቸው በማይታወቅ ወህኒ ቤት የሚገኙት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ስም፤ አቶ በረከት ስምዖን እና ሌሎች ተባባሪዎቻቸው በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ስም መፅሐፍ ለንባብ ሊያበቁ እያዘጋጁ መሆኑን ሚኒስትሩ አምልጧቸው የነገሩን ይመስለኛል፡፡ የመፅሐፉም ይዘት የኢህአዴግን “ልማት በማድነቅ” ፣ የተቃዋሚዎችን ስህተት፣ በተለይ የትጥቅ ትግል እያደረጉ ያሉትን እነ አርበኞች ግንቦት 7፣ ኦነግ፣ ትህዴን፣ አዴኃን፣ ኦብነግ፣ሲአግ፣አርዱፍ፣ … ወዘተ ድርጅቶችን በማብጠልጠል ላይ ተንተርሶ፤ አቶ አንዳርጋቸው ራሳቸውን ተሳስተው እንደነበርና በመፅሐፉ ይቅርታ ጠየቁ የሚል አዝማሚያ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል፡፡ በዚህም የተወሰነ የፖለቲካ ድል ለማግኘትና ተቃዋሚዎችንም ለመምታት እንደ አንድ መንገድም ሊጠቀሙበት ያሰቡም ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ጨወታው የዓለም አቀፉን በተለይም የአውሮፕንና የእንግሊዝን ዲፕሎማሲያዊ ጫና ለማርገብና ኢትዮያውያንን ለማታለል የታሰበ እንጂ፤ አካላዊና አዕምሯዊ ነፃነት ተነፍገው ባሉበት ሁኔታ አቶ አንዳጋቸው መፅሐፍ ይፅፋሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡

እውነት ህወሓት/ኢህአዴግ ርህራሄ ተሰምቶት አቶ አንዳርጋቸውንም ሆነ አሁንም በጅምላ እየታሰሩ ያሉትንና የታሰሩትን የፖለቲካ እስረኞች ለምን በነፃ አያሰናብትም?
በተለይ ለአቶ አንዳርጋቸው ላፕቶፕ ኮምፒዩተር ተፈቅዶላቸው መፅሐፍ እየፃፉ ወደማገባደዱ ላይ ናቸው ሲሉ ሚኒስትሩ አይደለም አቶ አንዳርጋቸው አንድ ተራ ደራሲም ሆነ ፀሐፊ በግፍ ላሰረውና እያሰቃየው ላለ ዘረኛ፣ ጨካኝና አረመኔ አገዛዝ በምን ሂሳብ፣ በምን የዋህነት ነው መፅሐፍ ፅፈው እየጨረሱ መሆናቸውን ሚናገሩት? ሌላው ቀርቶ የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሩ የነበሩት አቶ ተፈራ ዋልዋ ባለቤትና የአቶ አንዳጋቸው ጽጌ እህት ወ/ሮ አይኔ ጽጌ እንኳ እንዲገበኟቸው ባልተፈቀደበት፣ አዲስ አበባ ከሞላ ቤተሰብና ወዳጆቻቸው እንኳ አንድ ሰው እንዲገበኝ ባልተፈቀደበት፤ ላፕቶፕ ተፈቅዶ መፅሐፍ እየፃፉ ነው መባሉ፤ አቶ አንዳርጋቸው ላይ ሌላ ሴራ እየተሰራ ነው ወይም ተሰርቶ አልቆ አደባባይ ሊያበቁት ተዘጋጅተዋል ማለት ነው፡፡

ቴድሮስ አድሃኖም

ቴድሮስ አድሃኖም

3ኛው ጥርጣሬ፤ አይበለውና* በአሁን ሰዓት ኢህአዴግ አቶ አንዳርጋቸው ላይ እጅግ ጭካኔ የተሞላበት ምርመራ በሚያደርግበት ወቅትም ይሁን ሆን ብለው ህይወታቸው ላይ ከባድ አደጋ አድርሰው በስማቸው እጅግ የረከሰና ለኢህአዴግ አመራሮች የሚመጥን አስተሳሰብ ለገበያ ካቀረቡ በኋላ፤ አቶ አንዳርጋቸው በህመም ምክንያት አሊያም ራሳቸው ላይ በወሰዱት ርምጃ እንደተጎዱ ተደርጎ ድራማ ሊሰራ አሊያም ተሰርቶ አልቆም ሊሆን ይችላል ብሎ መገመት እንደ ሟርት ሊቆጠር አይችልም፡፡ ምክንያቱም አቶ አንዳርጋቸውን ለመግደል አስመራ ድረስ ትልቅ ተልዕኮ ተሰንቆ መክሸፉ የአደባባይ ምስጢር በሆነበት እና እጅግ ለሚፈሩትና አጥብቀው ለሚፈልጉት አንዳርጋቸው እውነትም ራርተው ከሆነ ይልቀቋቸውና ርህራሄያቸውን እንመን፡፡ ካልሆነም ቤተሰብና ወዳጅ ዘመድ እንዲሁም አድናቂዎቻቸው እንዲጎበኗቸው በይፋ ይፍቀዱና እንያቸው፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ላፕ ቶፕ ገብቶላቸው መፅሐፍ እየፃፉ ነው፣ ሊጨርሱ ነው…ማለት ከኋላው የተሰራና የተጠናቀቀ አሊያም ሊሰራ የታሰብ ሴራ መኖሩን ከማረጋገጥ ውጭ እውነት ነው ብሎ መቀበል በ24 ዓመታት ውስጥ ኢህአዴግን ካለማወቅ በሚመነጭ የዋህነት ካልሆነ መረጃውን ትክክል ነው ማለት ሞኝነት ይመስለኛል፡፡

በአጠቃላይ ጥርጣሬዬ ህወሓት/ኢህአዴግ እንደለመደው ስንኩል ፖለቲካዊ ሴራ ድራማውን ለማጠናቀር ይረዳው ዘንድ በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ስም መፅሐፍ እያዘጋጀ መሆኑን አሊያም አዘጋጅቶ መጨረሱን በጓዳ ርስ በርስ ሹክ የተባባሉትን አምልጧቸው እንደተናገሩት እቆጥረዋለሁ፡፡ ቢቻል በአሁን ወቅት የእንግሊዝ መንግሥት ስለ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ወቅታዊ ሁኔታ በአካል ሄዶ ማረጋገጥ እንዳለበትም መጠቆሙ የሚከፋ አይመስለኝም፡፡
ሌላው ሚኒስትሩ ጥሩ ናቸው በሚል ባይሆንም ስለ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በተናገሩት “መረጃ” ዙሪያ ማመስገኑ የሚከፋ አይመስለኝም፡፡ ለነገ የሚሆን መረጃ ጀባ ብለውናል ብዬ ስለማምን፡፡
በተረፈ አቶ አንዳርጋቸው ባሉበት ፈጣሪ ጠብቆ በሙሉ ጤንናትና ሰላም እናያቸው ዘንድ ተመኘሁ፡፡

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: