አዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ ሲኤምሲ በሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ምድብ ችሎት፤ ዛሬ ሐምሌ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. በ አቡበከር አህመድ የክስ መዝገብ ክስ ተመስርቶባቸው ከ3 ዓመታ በላይ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የነበረው የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ላይ የቅጣት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡ የኮሚቴው አባላትም ከ7 ዓመት እስከ 22 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት እና ለ5 ዓመታት ከማኀበራዊ መብቶቻቸውም እንዲታገዱ የቅጣት ውሳኔ መተላለፉ ተጠቁሟል፡፡
ዛሬ በተላለፈባቸው የቅጣት ውሳኔ የተላለፈባቸው 18ቱ የኮሚቴው አባላት፡-
አቡበከር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ያሲን ኑሩ እና ካሚል ሸምሱ እያንዳንዳቸው 22 ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡
በድሩ ሁሴን፣ ሳቢር ይርጉ፣ መሃመድ አባተ፣ አቡበከር አለሙ እና ሙኒር ሁሴን እያንዳንዳቸው 18 ዓመት እስር ሲፈረድባቸው፤
ሼህ መከተ ሙሄ፣ አህመድ ሙስጠፋ፣ ሼህ ሰኢድ አሊ ጁሃር፣ ሙባረክ አደም እና ካሊድ ኢብራሂም እያንዳንዳቸው 15 ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡
ቀሪዎቹ ሙራድ ሽኩር፣ ኑሩ ቱርኪ፣ ሼህ ባህሩ ኡመር እና ጋዜጠኛ ዩሱፍ ጌታቸው እያንዳንዳቸው 7 ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡
የዛሬውን ፍርድ በተመለከተም ድምፃችን ይሰማ ተቃውሞውን በመግለፅ፤ የሚከተለውን የትግል ስልት አጠናክሮ እንደሚቀጥል በመግለፅ 6 ነጥቦች ያሉት የአቋም መግለጫ ማውጣቱን ቢቢ ኤንን ጨምሮ የተለያዩ ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡
የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ ከመቋቋሙ በፊት በጥር 2004 ዓ.ም. ይፋ ጥያቄ መነሳት የጀመረው በአዲስ አበባ አወሊያ ትምህርት ቤት ጋር ተያይዞ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፤ የተጠ የቁ 3 መሰረታዊ ጥያቄዎች በወቅቱ ምላሽ ባለማግኘታቸው አሁን የተፈረደበት ኮሚቴ ሊቋቋም መቻሉንና ኮሚቴው አባላት ከመታሰራቸው በፊት በመፍትሄው ዙሪያ ከሚመለከታቸው የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ጋር በይፋ ውይይት ሲደረግ እንደነበር አይዘነጋም፡፡