አዳማ የኤድስ ተጠቂዎች ማደርያን ወደ መቅዲ ባርና ሬስቶራንት ቀየረች?!

የትነበርክ ታደለ
ይህ የምስራች እንዳይመስላችሁ! እጅግ ዘግናኝ አሳፋሪና አሳዛኝ የሀገራችን እውነታ ነው። ከአመታት በፊት ሀገር በኤች አይቪ የደረሰባትን የጭለማ ድባብ አንረሳውም! እርግጥ አሁንም ገና ከሀዘኑ ሙሉ በሙሉ አልተላቀቅንም። በዝያ የጭለማ ዘመን፣ መፍትሄ ከሀገር ውስጥም ከውጭም ሲፈለግ፣ ወጣቱ በየቦታው ሲረግፍ፣ ቤተሰብ ሲበተን አዳማ ውስጥ አንድ ሰው ተገኘ።

መስፍን ፈይሳ (የመስፍነ ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት መስራች)

መስፍን ፈይሳ (የመስፍነ ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት መስራች)

ይህ ሰው መስፍን ፈይሳ ይባላል። መስፍን ራሱም የቫይረሱ ተጠቂ መሆኑን ይፋ አውጥቶ በመናገር የሱ ቢጤ ወገኖቹን ለመርዳት ቆርጦ ተነሳ። እሱ እንደሚናገረው ማዳበርያ ከረጢት አንገቱ ላይ አስሮ በየደጃፉ እየዞረ ምግብ እየለመነ የሰበሰባቸውን ወገኖቹን መመገብ ያዘ።

እየቆየ ጥረቱ ፍሬ አፍርቶ በሀገር አቀፍ ደረጃ እውቅና የተሰጠውና ከ5000 ሰዎች በላይ የተረዱበት “መስፍን ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት” ተቋቋመ።

ይህ ተቋም አሁን “መቅዲ ባርና ሬስሮራንት ተብሎ ወጣቶች ቀንና ለሊት የሚጨፍሩበት፣ በሺሻ ጢስ የሚታጠኑበትና ህልማቸውን የሚነጠቁበት ቦታ ሆኗል።

ከሰአታት በፊት ግለሰቡ በፌስ ቡክ ገጹ ላይ በለቀቀው ቪዲዮ እንዳስታወቀው በጉልበት ከሀገር እንድወጣ ካደረጉኝ በኋላ ተቋሙን አፈራርሰው አራት ሚሊየን የሚገመት ንብረት ዘርፈው ጉዳተኞቹን በትነው ህንጻውን ከኤች አይቪ መከላከያነት ወደ ማሳራጫነት አዙረውታል ብሏል።

እጅግ የሚደንቀው ደግሞ ይህ ተቋም (አሁን መቅዲ ባር) የሚገኘው ከአዳማ ዩኒቨርስቲ አጠገብ መሆኑ ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለያዩ አለማቀፍ ሚዲያዎች እንደሚዘግቡት ሀገራችን ውስጥ ዝሙት በርካሽ የሚሸጥባቸው ስፍራዎች ዩኒቨርስቲዎች ባሉበት አካባቢ ነው።

በተለይ ደግሞ አዳማ ናዝሬት በዚህ ግምባር ቀደም ተጠቃሿ ናት። አንድ የቅርብ ጊዜ መረጃ እንደሚያሳየው አዳማ 230.000 ነዋሪዎች ያላት ስትሆን ከዚህም ውስጥ ካሉት ሴቶች 5000 ዝሙት አዳሪዎች ናቸው። ይህም ማለት ከመቶ አምስት ፐርሰንቱ በዚሁ ስራ የሚተዳደሩ ናቸው። ልብ በሉ ይህ ቁጥር የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን አይጨምርም።

እንግዲህ ይህንን አይነት ጉድ የተሸከመች ከተማ እንዴት ባለ አስተዳደር እጅ ብትወድቅ ነው የህዝብን ሁለንተናዊ ጤንነት ከመጠበቅ ሀላፊነቱ እየሸሸ በግለሰብ የተቋቋመ ተቋም ለማፈረስ የተደፈረው?

እጅግ በጣም የሚገርመው ደግሞ ይህ ተቋም ሲጀመር የመሰረት ድንጋይ የጣሉት በአሁን ሰአት የክልሉ ፕሬዚዳንት የሆኑት ኦቦ ሙክታር ከድር መሆናቸው ነው። (አቡነ ጳውሎስም በቦታው ነበሩ)

Mesfin Feyisa Initiative adama-nazereth

እና ምነው? ኦቦ ሙክታር አዳማ ውስጥ ምን እየተካሄደ ማወቅ አይችሉም ማለት ነው? ለአንድ ትልቅ አላማ ራሳቸው በቦታው ድረስ ሄደው መሰረት የጣሉለት ተቋም እጅግ በሚያሳፍርና በሚያዋርድ ሁኔታ ተሽቆልቁሎ ሲጠፋ ምንም አልሰሙም ማለት ነው? አዳማ የኦሮሚያ ዋና ከተማ ነች! ይህንን ሳይስሙና ሳያዩ ወለጋ ጫፍ ወይም አርሲ ቦረና ስላለው እንዴት ሊሰሙ ይችላሉ? ነው ወይስ በዚህ ጉዳይ ላይ የሳቸው ይሁንታ አለበት? እውነት ለመናገር መልስ ሊሰጡበት የሚገባ ጥያቄ ነው።

የአዳማ ህዝብስ ቢሆን በራሱ ጉዳይ ላይ ከሱ የተሻለ ማን ሊጠይቅለት ይችላል? ግለሰቡ እንደተናገሩት ወደዚህ ባርና ሬስቶራንት ልጆቻችሁ እየሄዱ እያያችሁ ዝም ብትሉ በልጆቻችሁ ህይወት ላይ ፈርዳችኋል።

መንግስትም ቢሆን እነ መቄዶኒያን የመሳሰሉ ወገንን ከጎዳና የሚሰበስቡ ተቋማት ነገ በተመሳሳይ መንገድ እንደማይፈርሱና ወደ ሺሻ ቤትነት እንደማይቀየሩ ምን ማስተማመኛ ይሰጠናል? ትውልድ እየጠፋ ነው! ህግ እየተጣሰ ነው! የምንፈልገውን እያጣን የማንፈልገው እየተጫነብን በዚህ ላይ ለጩሀታችን ዝምታ እየተመለሰልን ነው! ነገ አጣብቂኙ ለሀገር ነውና መቅዲ ባር በአስቸኳይ ወገኖቻችን ወደ ሚረዱበት ተቋምነት ይመለስልን! ወገን በጭፈራ ቤት አይታከምም!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: