የኢትዮጵያ ድርቅና ርሃብ ትናንት እና ዛሬ

ብስራት ወልደሚካኤል

በርግጥ ድርቅ በተፈጥሮ ሊከሰት የሚችል የአየር መዛባት አደጋ ውጤት ነው፡፡ ድርቅ ባለፀጋም ሆነ እንደኛ ባሉ ደሃ ሀገራት ሊከሰት ይችላል፡፡ የድርቁ መንስኤም ተፈጥሯዊ አሊያም ሰው ሰራሽ ሊሆን ይችላል፡፡

Ethiopia_drought_cows

ርሃብ በምግብ እጥረት የሚከሰት ሲሆን፤ መንስዔውም የምርት አቅርቦት ማነስ አሊያም የምግብ ፍላጎት ከምርት አቅርቦት ጋር አለመጣጣም ሊሆን ይችላል፡፡ የዚህ ዋነኛ ምክንያት ደግሞ ፍላጎት እና አቅርቦትን አሊያም የሀገር ምርት ለማሳደግ ሀገሪቱ የምትከተለው ፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡ በኢትዮጵያም በተለያዩ መንግሥታትም ሆነ ዘመን ድርግቅን ተከትሎም ይሁን ያለድርቅ ለተከሰቱት እና እየተከሰቱ ላሉ ችግሮች ዋነኛ መንስዔው ፖለቲካዊ የፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡

ርሃብ በተፈጥሮ የሚከሰት ሳይሆን የሀገሪቱ መንግሥት ስርዓት በሚከተለው የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡ ደካማ ወይም ተፈጥሮንና የሀገሪቱን ህዝብ አቅምና ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም ፖሊሲ ትግበራ ባለበት ሀገር ድርቅ ከተከሰተ ምንጊዜም ርሃብ አለ፡፡ ርሃቡ ምንም እንኳ ድርቅን ተከትሎ የመጣ ቢሆንም ዋነኛ ምክንያቱ ግን የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡

በሀገራችን በተከታታይ የተከሰተውም ርሃብ ዋነኛ ምክንያት ድርቁ ሳይሆን የደካማ ፖሊሲ ውጤት ነው፡፡ ምክንያቱም ድርቅ የተከሰተባቸው ሀገሮች ሁሉ ርሃብ አይከሰትም፡፡ ደካማ ፖሊሲ ያለባቸው ሀገሮች ግን ድርቅ ካለ ምንም ጊዜም ርሃብ አለና፡፡

በዘመናዊ ኢትዮጵያ የመንግሥት ታሪክ ጎልቶ መታወቅ የጀመረው በዳግማዊ አጼ ምኒልክ ዘመን ቢሆንም እስከዛሬም ይህን ችግር የሚቀርፍ የመንግሥት ፖሊሲና ተግባር አልታየም፡፡ አሳዛኙ ነገር በዘመነ ዳግማዊ ምኒልክ የነበረውን ርሃብ ለዓለም ማኀበረሰብ አሳውቆ ተገቢውን ርዳታ ይቆ ለተጎጂዎች በማድረስ ህይወት ለማትረፍ ቴክኖሎጂው ችግር ነበረብን፡፡ ቢሆንም ግን ይህን ክፍተት ንጉሱን ጨምሮ ባለሟሎቹ (አመራሮቹ) የተፈጠረውን ርሃብ በድርቅ ላይ ሳያመሃኙ ወዲያው ለህዝቡ በማሳወቅ ወገን ለወገን በሚችለው አቅም እንዲረዳዳ እና የመንግሥት ካዝና (ለችግር ጊዜ የተቀመጠ የእህል ጎተራ) ሳይቀር በይፋ ተከፍቶ ለተጎጂዎች ወዲያው እንዲደርስ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡ ይህ በጎ አስተሳሰብ ቢሆንም ከነበረው የእህል ክምችት አናሳነት እና የትራንስፖርት ችግር አኳያ ለሁሉም ተጎጂ እኩል ማድረስ ባይቻልም መንግሥት ችግሩን አምኖ የህዝቡን ድጋፍ ጤቆ ተገቢውን ምላሽ አግኝቶ ነበር፡፡ ቢሆንም ግን ብዙ ወገኖቻችንን በርሃቡ አጥተናል፡፡

Ethiopian famine 2015

በዘመነ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ የነበረው በ1965/66 ዓ.ም. ርሃብ ግን ንጉሱም ህዝቡም እንዳያውቁ መኳንንቱ ለመሸፋፈን ሞክረዋል፡፡ በዚህም መኳንንቱ ጠግበው እየበሉ በርካታ ወገኖቻችን በወቅቱ በተከሰተው ርሃብ ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ይሄ በተለይ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍለክ እጅግ የከፋ የታሪክ ጠባስም ጥሎልን አልፏል፡፡

በዘመነ ደርግ በተለይ በ1977 ዓ.ም. የተከሰተውን ልብ ይሏል፡ የተከሰተውን ርሃብ የሀገሪቱ መራሄ መንግሥት መንግሥቱ ኃይለማርያምና ሁሉም ሹማምንት ቢያውቁም ከሀገሪቱ ህዝብ (ርሃብ ካልነካቸውን) እና ከዓለሙ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ተሞክሯል፡፡ በዚህም ብዙ ወገኖቻችን በጊዜ ማዳን ሲቻል በሞት ተነጥቀናል፤የበለጠ ክብራችንም እንዲዋረድ በር ከፍቷል፡፡

በዘመነ ኢህአዴግ ከአንዴም ሶሰት ጊዜ፤በተለይ በ1985ዓ.ም.፣ 1986/87 ዓ.ም. እና የአሁኑን የ 2007/08 ዓ.ም. ርሃብ መንግሥት ከሀገሬው ህዝብና ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ሞክሯል፤ባይችልም፡፡ በቅርቡ በተለይም ባለፈው ክረምት በምስራቁ የሀገራችን ክፍል የተጀመረው ርሃብ ወደ ሰሜኑ እና መካከለኛው የሀገራችን ክፍል በፍጥነት ቢዛመትም መንግሥት በምግብ ራሳችንን ችለናል፣ ርሃብ አልተከሰተብ፣ …ወዘተ የሚለው ፈሊጥ አንድ ወር እንኳ አልሞላውም፡፡ ርሃቡ ልክ እንደሰደድ እሳት እና አውሎ ነፋስ ማዕበል ምስራቁን፣ ሰሜኑን እና ከፊል መሐከለኛ የሀገራችን አካባቢ በፍጥነት ተዛመተ፡፡ ርሃብ የለም፣ በምግብ ራሳችንን ችለኛል፣…የክፉዎች ወሬ ነው ሲባል የነበረው ርሃብ፤ አሁን መንግሥት በህዝብ ላይ እና በእንሰሳቶቻቸው ላይ ከፍተኛ እልቂ ከደረሰ በኋላ “ኢሊኖ በሚባለው ድርቅን ተከትሎ በነሳው ርሃብ አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር 5 ሚሊዮን አካባቢ ደርሷል፣ ከዓለም አቀፉ ለጋሽ ድርጅቶች እና ሀገራት አፋጣኝ እና በቂ ድጋፍ አላገኘንም,…” የሚል ይፋ ልመናዊ መግለጫ ተሰጠ፡፡ የተራቡ ወገኖቻንን ቁጥር መገመትና መናገር ቢከብድም አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ግን ከ 10 ሚሊዮን በላይ እንደሚሆን ይገመታል፡፡

በጣም የሚያሳዝነው ሁሉም ስርዓቶች በተፈጥሮ ሃብትና በግብርና ላይ ያላቸው ፖሊሲ የአንዳቸው ከአንዳቸው የማይሻል፣ ያልተለየ ቢሆንም በዳግማዊ ምኒልክ ጊዜ ግን ርሃብ ለመደበቅ አልተሞከረም፤ ይልቁንም ከመንግሥት ካዝና በተጨማሪ ህዝቡ እንዲረዳዳ የጠማፅኞ ጥሪ ተደረገ እንጂ፡፡ በኃይለስላሴ ዘመንም ቢሆን ሹማምንቱ ከንጉሱ እና ርሃብ ካልደረሰበት ህዝብ ለመደበቅ ቢሞከርም መደበቁ አልቻሉም፡፡ የደርግና ኢህአዴግ ስርዓት ክፋት ግን ከበታች ሹም እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ድረስ ርሃቡን እያወቁ ለመደበቅ መሞከራቸው የፖሊሲ ችግራቸውን ለመደበቅ ከመሞከራቸው ይልቅ በሰብዓዊ ፍጡር ህይወት ላይ ያላቸውን ጭካኔ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም ርሃብ ቀን አይሰጥምና፡፡ ርሃብ የሰውንም ሆነ የእንሰሳትን ህይወት ሲቀጥፍ ዳግም አናገኛቸውምና፡፡

አሁን ርሃቡ በዋነኛነት የተከሰተው ውሃ ቅዳ ውሃ መለስ የሆነው የመንግሥት ስርዓትና በመሪዎች ቸልተኝነት፤ የተፈጥሮ ሃብት፣ የመሬት፣ ስነ ህዝብ፣የምግብ እና የመረጃ ጥንቅር ፖሊሲ ችግር ነው፡፡ ባለፈው ከነበረው ችግር ለነገው አለመማራችን እና ለመማር አለመዘጋጀታችን ውጤትም ነው፡፡ ስለዚህ ርሃብን እና የተራበውን ህዝብ ቁጥር በመደበቅና በማዛበት ርሃብን ማቆም እንደማይቻል ልናውቅ ይገባል፡፡ ስለዚህ በርሃብ የተጎዱ ወገኖቻችንን በተመለከተ የውጭ መንዛሪ እጠረት ለመሸፈን ባለመ የውጭ ለጋሽ ሀገሮችን ተማፅኞ ብቻ ሳይሆን ዜጎች ወገኖቻችንን እንዲረዳዳ ዕድሉ ሊሰጥና በይፋ የምግብና ቁሳቁስ ድጋፍ ማሰባሰብ ስራ በማድረግ የወገኖቻችንን ህይወት መታደግ ይቻላል፡፡ ለዚህም ጊዜ ሊሰጠው አይገባም፤ ርሃብ ጊዜ አይሰጥምና፡፡

ከፖሊሲ ችግር አንዱ ከዝናብ ጥገኝነት ለመውጣት የሚያስችል መስኖ አለማስፋፋት፣ የመሬት ባለቤትነት፣ የሜትሪዮሎጂ ተቋም ብቃት ባላቸው የአየር ትንበያ ባለሙያዎች አለመዋቀር እና አለመጠናከር፣ መስኖ በሌለባቸውና ዓመታዊ የዝናብ መጠናቸው ዝቅተኛ የሆኑ ቆላማ አካባቢዎች የተለየ ትኩረትና ጥንቃቄ እንዲሁም በቂ የእንሰሳትና የሰው ህክምና እና የምግብ ቅድመ ዝግጅት ክምችት አለማድረግን መጥቀስ ይቻላል፡፡

ከአስቸኳይ ርስበርስ የመረዳዳት እና ዓለም አቀፍ ድጋፍ ጥየቃ እንቅስቃሴው እንዳለ ሆኖ፤ ለ24 ዓመታት ተሰርቶበት ለውጥ ያላመጣውን ፖሊሲም ማሻሻል አሊያም መቀየር ዋነኛው ቁልፍ ተግባር መሆን አለበት፡፡ አለበሊያ በኢህአዴግ ዘመን ለ4ኛ እና 5ኛ ጊዜ መከሰቱ እንደማይቀር የአሁኑን ጨምሮ ያለፉት ጊዜያት ከበቂ በላይ አስተማሪዎች ናቸውና ከፖለቲካ ጋጋታ ትርፍ ይልቅ ሕይወት የማዳኑ ተግባር ሊፈጥን ይገባዋል፡፡

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: