እነ ሀብታሙ አያሌው በጠቅላይ ፍርድ ቤት የቃል ክርክር አደረጉ

ኢዩኤል ፍስሃ ዳምጤ

“እኔ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል እንደመሆኔ መጠን የኢህአዴግን ጭቆና ማጋለጥ ግዴታዬም መብቴም ጭምር ነው! ይህን ካላደረጉ ምኑን ተቃዋሚ ሆንኩ?” አብርሃ ደስታ
“እኔ አሸባሪ አይደለሁም! የታሰርኩት በኢህአዴግ የፖለቲካ ሴራ ነው! እኔ የፖለቲካ እስረኛ ነኝ!” ዳንኤል ሺበሺ

Political prisoners

 

በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው በሥር ፍርድ ቤት ውሳኔ በነፃ የተሰናበቱት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ አቶ የሺዋስ አሰፋና በተመሳሳይ የክስ መዝገብ ውስጥ ከአመራሮቹ ጋር የተከሰሰው አቶ አብርሃም ሰለሞን በፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ዛሬ ታህሳስ 15 ቀን 2008 ዓ.ም በመቅረብ የቃል ክርክር አድርገዋል፡፡
በችሎቱ የተሰየሙት ግራ ዳኛ መዝገቡ ለዛሬ የተቀጠረው ታህሳስ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ተከሳሾቹ የፍርድ ቤቱ ሰብሳቢ ዳኛ የሆኑት አቶ ዳኜ መላኩ ከሰብሳቢነታቸው እንዲነሱ ባቀረቡት የፅሁፍ አቤቱታ ላይ መልስ ለመስጠት፤ የተከሳሾቹንና የአቃቤ ሕግን የቃል ክርክር ለማድመጥ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ተከሳሾቹ “ሰብሳቢው ዳኛ ይነሱልን!” ብለው ያቀረቡት ጥያቄ ፍ/ቤቱ ስላላመነበት ውድቅ መደረጉን ገልፀዋል፡፡

አቃቤ ሕግ በችሎቱ ባቀረበው የይግባኝ አቤቱታው ተከሳሾቹ ከግንቦት ሰባት አመራር አባላት ጋር በተለያየ ጊዜ መገናኘታቸውን፤ ይህንንም የሚያስረዳ ማስረጃ ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ማቅረባቸውን ነገር ግን የስር ፍርድ ቤቱ እነዚህን ማስረጃዎች ሳይመዝን “በደፈናው ውሳኔ ስለሰጠ” ይግባኝ መጠየቃቸውንና የስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ሲሰጥ ከጭብጥ መውጣቱን ገልጿል፡፡ “ፍርድ ቤቱ ከፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ አንቀፅ 23 መሰረት የቀረበውን የሰነድ ማስረጃዎች በመመልከት የስር ፍርድ ቤት ውሳኔን በመሻር ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን ክስ እንዲከላከሉ ፍርድ ቤቱ ይወስንልን ዘንድ እንጠይቃለን” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡

1ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ አያሌውና 5ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን በጠበቃቸው አምሃ መኮንን በኩል የመከራከሪያ ሃሳባቸውን አቅርበዋል፡፡ አቶ አምሃ መኮንን የስር ፍርድ ቤቱ ደምበኞቻቸውን በነፃ ሲያሰናብታቸው የቀረቡትን ማስረጃዎች መዝኖ መሆኑን ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡ አቃቤ ሕግ በክሱ ላይ ያቀረባቸው ነገሮች እንደመረጃ እንጂ እንደማስረጃ ሊያዙ እንደማይገባ የተከሳሾቹ የቀድሞ ጠበቃ በስር ፍርድ ቤት ክርክር አድርገው የስር ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 2 ቀን 2007 ዓ.ም “በማስረጃ ሊያዙ ይገባል!›› ብሎ ብይን ማስተላለፉን አቶ አምሃ አውስተዋል፡፡

ጠበቃው ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ በኩል የሚቀርቡ ማስረጃዎችም ፍርድ ቤት ሊመረምራቸው እንደሚገባ ሲያስረዱ፡- “የብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ በኩል የሚቀርቡ መረጃዎችን ፍርድ ቤቱ ሙሉ ለሙሉ የሚቀበል ከሆነ የፍርድ ቤቱ ሚና ምን ሊሆን ነው? ፍርድ ቤቱ ከተቋሙ በኩል የሚቀርቡለትን መረጃዎች ሙሉ ለሙሉ የሚቀበል ከሆነም ፈራጁ ፍርድ ቤት ሳይሆን ብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ነው” በማለት አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

ደምበኛቸው አቶ ሀብታሙ አያሌውም በክሱ ላይ ‹‹ዘመነ ካሴ›› ከተባለው የግንቦት ሰባት አባል ጋር በመነጋገር አብረው ለመስራት ተስማሙ ተብሎ ቢገለፅም ይህን የሚያስረዳ ማስረጃ አለመቅረቡን ገልፀዋል፡፡ ደምበኛቸው ከግለሰቡ ጋር ባደረጉት የስልክ ልውውጥ አንድም ቦታ ላይ አብረው ለመስራት መስማማታቸውን እንዳልገለፁ ጠበቃው ጠቁመዋል፡፡ በክሱ ላይ የአንድነት ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ የሆነው አቶ ሀብታሙ አያሌው ከዘመነ ካሴ ጋር ግንኙነት አደረጉ ተብሎ የተገለፀው ከእውነታ የራቀ መሆኑን ጠበቃው ገልፀዋል፡፡ በተጠቀሰው ጊዜ አቶ ሀብታሙ አይደለም የአንድነት ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሊሆኑ ቀርተው፤ የፓርቲው አባል እንዳልነበሩም አቶ አምሃ አስረድተዋል፡፡ አቶ ሀብታሙ በበኩላቸው በክሱ ላይ ተከሳሽ በዚህ የሞባይል ቁጥር ግንኙነት አድርጓል ተብሎ አለመገለፁን የስልክ ልውውጡም ምን እንደሆነ የሚያስረዳ አንዳች ነገር አለመቅረቡን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

Abreham Solomon

አቶ አምሃ ደምበኛቸው በሆነው 5ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን ላይ ምንም አይነት የሰነድ ማስረጃ አለመቅረቡን የግንቦት ሰባት አባል ነው ሲባልም፤ በግንቦት ሰባት መዋቅር ውስጥ እንዳለ የሚያሳይ ማስረጃ አለመቅረቡን ደምበኛው በምንም አይነት የሽብርተኝነት ተግባር ላይ እንደተሰማራ የሚገልፅ ምንም አይነት ማስረጃ አለመቅረቡን ገልፀዋል፡፡ አቶ አብርሃም ሰለሞን በበኩሉ ያለአንዳች ማስረጃ መታሰሩን ሲያስረዳ፡- “ከታሰርኩ በኋላ ነው ማስረጃ ሲፈለገብኝ የነበረው፤ ከታሰርኩ በኋላም ቤቴ እንኳ አልተፈተሸም፡፡ መንግስት አሰረኝ ብዬ አላምንም ያሰረኝ አንድ ግለሰብ ነው” ሲል ተደምጧል፡፡

2ኛ ተከሳሽ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ 3ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃ ደስታና 4ኛ ተከሳሽ የሺዋስ አሰፋ ያለጠበቃ በመቆም በግል ክርክራቸውን ያካሄዱ ሲሆን፤ ሶስቱም ተከሳሾች የአቃቤ ሕግ የይግባኝ ማመልከቻ ላይ እነሱን የሚመለከት ቅሬታ አለመቅረቡን ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል፡፡ አቶ ዳንኤል ሺበሺ “እኔ አሸባሪ አይደለሁም! የታሰርኩት በኢህአዴግ የፖለቲካ ሴራ ነው! እኔ የፖለቲካ እስረኛ ነኝ!” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ የቃል ክርክር ለማድረግ ያዘጋጁት ወረቀትም በማረሚያ ቤቱ እንደተቀደደባቸው ለፍርድ ቤቱ አሳይተዋል፡፡ ወረቀቱ ማህተም የተደረገበት ቦታ ተቀዶ መውጣቱን በችሎቱ ለነበሩ ታዳሚያን በግልፅ ታይቷል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃ ደስታም ከታሰሩ በኋላ ማስረጃ ሲፈልግባቸው እንደነበርና በብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ የሚቀርብ መረጃ በፍርድ ቤት ሳይመዘን ሙሉ ለመሉ ተቀባይነት የሚያገኝ ከሆነ ተቋሙ ከሳሽም፣ መስካሪም፣ ዳኛም ሆነ ማለት ነው፡፡ ይህ ከሆነ ዘንድ ደግሞ ፍርድ ቤት መምጣትም አያስፈልግም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ በክሱ ላይ ለኢሳት ቴሌቪዥን ቃለምልልሰ ሰጠ ተብሎ የቀረበው ክስ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ሲያስረዱ፡- “እኔ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል እንደመሆኔ መጠን የኢህአዴግን ጭቆና ማጋለጥ ግዴታዬም መብቴም ጭምር ነው! ይህን ካላደረጉ ምኑን ተቃዋሚ ሆንኩ?” በማለት ለፍ/ቤቱ የገለፁ ሲሆን፤ በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ በመቅረብ ሃሳባቸውን ሲገልፁ የነበሩትም የኢህአዴግን ጭቆናን ማጋለጥ መብታቸው በመሆኑ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

4ኛ ተከሳሽ አቶ የሺዋስ አሰፋ በእሳቸው ላይ የቀረበ አንድም የሰው ምስክር እንደሌለ ገልፀው፤ ማዕከላዊ በነበሩበት ወቅትም በምርመራ ላይ አንድም ቀን ስለግንቦት ሰባት ተጠይቀው እንደማያውቁ ምርመራ ላይ ሲጠየቁ የነበሩትም ስለ ሰማያዊ ፓርቲ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ አቶ የሺዋስ የሰማያዊ ፓርቲ አባል በመሆናቸው ብቻ አያሌ መከራዎችን እየተጋፈጡ እንደሚገኙ ለፍ/ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ያለፉትን 6 ወራት በማንም አለመጎብኘታቸውን ለፍ/ቤቱ ገልፀዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የቃል ክርክሩ በፅሁፍ ተገልብጦ ከቀጣይ ቀጠሮ በፊት ከመዝገቡ ጋር ተያይዞ እንዲቀርብ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ 1ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ አያሌው የሚገኙበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ተከሳሹ ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ታህሳስ 19 ቀን 2008 ዓ.ም መልስ እንዲሰጥ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ የማረሚያ ቤት ተወካዩ በተጠቀሰው ቀን አቶ ሀብታሙን ይዞ እንዲቀርብ ፍርድ ቤቱ አዟል፡፡

የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክር መዝኖ ውሳኔ ለመስጠት ለታህሣሥ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ እነ ሀብታሙ አያሌው ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ከተመሰረተባቸው የሽብርተኝነት ክስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ውሳኔ ማስተላለፉ አይዘነጋም፡፡

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: