የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ዛሬ ታህሣሥ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ለስራ ከቤቱ ሲወጣ በፌደራል ፖሊሶችና በደህንነት ሰዎች ተይዞ ታስሯል። የፀጥታ ኃይሉ መኖሪያ ቤቱን ከፈተሹ በኋላ ፣ጋዜጠኛውን ወደ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል ማዕከላዊ መስደው ማሰራቸው ቢገለፅም፤ መንግሥት ጋዜጠኛውን ለምን እንዳሰረ የገለፀው ነገር የለም፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ ከመሆኑ በተጨማሪ የእንቁ መፅሔትም ፀሐፊ እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን፤ ከዚህ በፊት በመንግሥት ኃይሎች ከፍተኛ ማስፈራሪያና ዛቻ ይፈፀምበት እንደነበርም ታውቋል፡፡ጌታቸው ነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣን እና ደረ- ገፅን ጨምሮ በተለያዩ ድረ-ገፆችና የራሱ ማኀበራዊ ገፅ ላይ የተለያዩ ሐሳቦችን ይፅፍ እንደነበርም ይታወቃል፡፡
ከጋዜጠኛ ጌታቸው በተጨማሪ በተደጋጋሚ ሲታሰሩና ሲፈቱ የነበሩት ሶስቱ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት መካከል ዳንኤል ተስፋዬ፣ ኤርምያስ ፀጋዬ እና ቴዎድሮስ አስፋው ዛሬ መታሰራቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡
በተመሳሳይ ዜና ባለፈው ቅዳሜ ታህሣሥ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት አዲስ አበባ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ በፀጥታ ኃይሎች ተይዞ የታሰረውና የኦሮሚያ ሬዲዮናቴሊቪዥን ዜና አንባቢ ጋዜጠኛ ፈቃዱ ምረከና አለመፈታቱ ታውቋል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ጋዜጠኛ ፈቃዱ ምርከናም ሆነ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በምን ምክንያት እንደታሰሩ ከመንግሥት በኩል የተገለፀ ነገር የለም፡፡
ከጋዜጠኛ ፈቃዱ እና ጌታቸው በተጨማሪ በርካታ ጋዜጠኞች በእስር ላይ እንደሚገኙና በዓለም አቀፍ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋቾች ድርጅቶች፤ ኢትዮጵያም ጋዜጠኞችን በማሰር ከአፍሪካ የሁለተኛ ደረጃን ተቀዳጅታ እንደነበር አይዘነጋም፡፡