ባለፈው ሳምንት ጥር 19 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል በተከሰተው የብሔር ግጭት ከ40 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተሰምቷል፡፡ የግጭቱ መንስኤ እስካሁን በገለልተኛ አካል ባይታወቅም ግጭቱ በክልሉ ነዋሪ በሆኑ አኝዋክና ኑዌር ማኀበረሰብ መካከል በተፈጠረ ግጭት እንደሆነ ይነገራል፡፡
የማዕከላዊ መንግሥት ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩሉ የሟቾች ቁጥር 14 ነው ግጭቱም በቁጥጥር ስር ውሏል ቢሉም፤ የጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ኢታንግ ወረዳ አስተዳደር አቶ ኦኬሎ ኦባንግ በበኩላቸው ብዙ ሰዎች እንደሞት እንደሚነገርና በአሁን ወቅት የሟቾችን ቁጥር በርግጠኝነት መግለፅ እንደማይቻል ለብሉንበርግ ተናግረዋል፡፡
ለግጭቱ ምክንያት ሊሆን ይችላል ተብሎ የተገመተው በአካባቢው የደደቡብ ሱዳን አማፂ መሪ ሬክ ማቻር ደጋፊ እንደሆኑ የሚነገርላቸው ከ264 ሺህ በላይ የኑዌር ጎሳዎች በክልሉ ኢታንግ ወረዳ መስፈራቸውና በአካባቢው ማኀበራዊ መስተጋብር ላይ ተፅዕኖው እየበረታ ነው በሚል እንደሆነም ቢነገርም ከመንግሥትም ሆነ ከዓለም አቀፉ ስደተኞች ድርጅት ስደተኞቹ አሳድረዋል ስለተባለው ተፅዕኖ የተገለፀ ነገር የለም፡፡
የተፈጠረውን ግጭት ተከትሎ በአካባቢው የፀጥታ ኃይሎች እና በማኀበረሰቡ መካከልም አለመግባባቶች እንደተፈጠሩ በዚህም በርካታ ሰዎች መጎዳታቸውን እና የመኖሪያ ቤቶች መቃጠላቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
ከግጭቱ ጋ በተያያዘም በርካታ ሰዎች በክልሉ ዋና ከተማ ጋምቤላ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውንና ጉዳት የደረሰባቸው የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡