በደቡብ ክልል ከዚህ ቀደም በልዩ ወረዳ አስተዳደር የነበረና በአሁን ወቅት የሰገን አካባቢ ዞን ስር ወደ ወረዳ አስተዳደርነት እንዲወረድ የተደረገው የኮንሶ ማኀበረሰብ አባላት የዞን አስተዳደር መዋቅር እንዲፈቀድላቸው መጠየካቸውን ተክትሎ በመንግሥት ተጣቂዎች በተወሰደ እርምጃ በግብርና የሚተዳደሩ ሁለት ሰዎች ተገድለዋል፡፡
እሁድ መጋቢት 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀትር ላይ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት አቶ ሞሌ አዛዥ እና አቶ ፋንታዬ ጊዮርጊስ በግብርና ሙያ የሚተዳደሩ ጎልማሶች እንደሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከተገደሉት በተጨማሪ 3 ሰዎች በፀኑ የቆሰሉ ሲሆን፤ ማኀበረሰቡም የተገደሉ 2 አስከሬኖች ይዞ ወደ ካራት አደባባይ በመውጣት ከፍተኛ ተቃውሞ ማሰማቱ ታውቋል፡፡
የአዲስ ሚዲያ መረጃዎች እንዳረጋገጡት፤ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ አሁንም በኮንሶ በርካታ የደቡብ ልዩ ፖሊስ ኃይል የደንብ ልብስ የለበሱ ፖሊሶች በኮንሶ ዋና ከተማ ካራት እና በተለያዩ የገጠር ቀበሌዎች ጭምር እንደሰፈሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የህዝባዊ ተቃውሞ ዋነኛ ምክንያት 55ሺህ የኮንሶ ማኀበረሰብ ስምና ፊርማ ያለበት ስምምነት ወደ ዞን አስተዳደር እንደግ የሚል ጥያቄ ከደቡብ ክልል እስከ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ማስገባታቸውና መንግሥትም በሐረገ-መንግሥቱ መሰረት ተገቢውን መልስ ሳይሰጥ ከልዩ ወረዳነት ወደወረዳነት በማውረድ ጥያቄያቸው ምላሽ ባለማግኘቱ በተፈጠረ አለመግባባት እንደሆነ ታውቋል፡፡ ተቃውሞንም ተከትሎ የኮንሶ ባህላዊ ንጉስ ካላ ገዛኸኝ ወልደ ዳዊትን ጨምሮ ከ200 ያላነሱ የአካባቢው ዜጎች መታሰራቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ መንግሥት የሰጠው ይፋዊ ምላሽ ባይኖርም በአካባው ከፍተና ውጥረት መኖሩን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡