በእነ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ ከ600 ቀናት በላይ ፍርድ ቤት ሲመላሱ የቆዩት ተከሳሾች ላይ ዛሬ ብይን ተሰጥቷል፡፡ በዚህም መሰረት አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ሰለሞን ግርማ ፣ መምህር ተስፋዬ ተፈሪ ጥፋተኛ ተብለዋል፡፡ በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ባህሩ ደጉ እና ዬናታን ወልዴ በነጻ ተሰናብተዋል፡፡
በተመሳሳይ የክስ ፋይል አብረው የተከሰሱት የፓቲካ ፓርቲ አመራሮች ( አብርሃ ደስታ ፣ ሃብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ የሸዋስ አሰፋ) እና መምህር አብርሃም ሰለሞን መከላከል ሳያስፈልጋቸው ነጻ መባላቸው ይታወሳል፡፡
ለአራት ወር ለሚጠጋ ጊዜ ማእከላዊ ምርመራ የከረሙት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው እና አብረው የታሰሩ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስና የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ተጨማሪ አንድ ሳምንት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ እስካሁን ድረስ በሽብር ከመጠርጠር ውጪ ክሳቸው በውል ያልታወቀው ፣ አቶ በቀለ ገርባ ፣ አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራውን ጨምሮ ኦሮሚያ ላይ የተነሳው ህዝባዊ አመጽ ተከትሎ ለእስር መዳረጋቸው ይታወሳል፡፡
ባለፈው ሳምንት ፍርድ ቤት ቀርበው ለዛሬ ክሳቸው እዲነበብ የተቀጠሩት 33 በአዲስ አበባ ከተማ ቦሌ ቡልቡላ አካባ ኦነግ ተዋጊነት የተጠረጠሩት እነ ሃብታሙ ሚልኬሳ ዛሬም ክሳቸው ሳይሰማ ለሚያዝያ 20 ሌላ ቀጠሮ እንዲቀርቡ ተላልፏል፡፡
ምንጭ፡- EHRP