በዚህ ሳምንት ውስጥ እንደሚጥል በተተነበየ ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ አማካይነት የአዋሽ ወንዝ ሞልቶ ጉዳት ሊያደርስ እንደሚችል፣ ብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አሳሰበ፡፡
ኮሚሽኑ ለሪፖርተር የላከው የቅድመ ማስጠንቀቂያ መልዕክት እንደሚገልጸው፣ ከሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ በስተቀር በአብዛኞቹ የአገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ እስከ ሚያዝያ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊጥል እንደሚችል፣ ከብሔራዊ የሚቲዮሮሎጂ ኤጀንሲ መረጃ ማግኘቱን ይጠቁማል፡፡
ከአዋሽ ተፋሰስ ባለሥልጣን በተገኘው ሌላ መረጃ መሠረትም የአዋሽ ወንዝ በቀጣዩ ሳምንት ሊሞላ ስለሚችል፣ ከዚህ ጋር ተያይዞ ጐርፍ በተፋሰሱ ባሉ አካባቢዎች ሊከሰት እንደሚችል መረጃዎች የሚያመለክቱ መሆኑን፣ በኮሚሽኑ የቅድሚያ ማስጠንቀቂያና ምላሽ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሙሉነህ ወልደ ማርያም ገልጸዋል፡፡
በመሆኑም በበቾ ወረዳ፣ በዓለም ጤና ወረዳ (ሁምቡሌና ጐሮ አካባቢዎች)፣ በስሬ ወረዳ፣ በወንጂ በተለይም በቆቃ ግድብ አካባቢ የሚኖሩ፣ በመርቲ ወረዳ፣ በመተሃራ (ፈንታሌ)፣ በአሚባራ፣ በዱለቻ፣ በገላአሎ፣ በገዋኔ፣ በተንዳሆ ግድብ አካባቢ የሚኖሩ፣ በአሳይታና በአፋምቦ ወረዳዎች የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጐርፍ ሊከሰትባቸው ስለሚችል ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ኮሚሽኑ አሳስቧል፡፡
የተጠቀሱት አካባቢዎች የመስተዳደር አካላትም በአካባቢዎቹ የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ከወንዙ በማራቅ ከጉዳት መጠበቅ እንዲችሉ የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉም አሳስቧል፡፡
ባለፈው መጋቢት ወር መጨረሻ በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በተከሰተው የጐርፍ አደጋ ከ20 ሰዎች በላይ መሞታቸው ይታወሳል፡፡
ብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን በ2008 ዓ.ም. የመጀመሪያ ወራት እንደ አዲስ የተቋቋመና በሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን የመከላከልና የቅድመ ማስጠንቀቅ ሥራ የማከናወን ኃላፊነት የተጣለበት ተቋም ሲሆን፣ ተጠሪነቱም በቀጥታ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ነው፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ