የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እነ ኦኬሎ አኳይ እስከ ዘጠኝ ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ቀጣ፡፡ ተከሳሾችም ሆኑ የፌደራል አቃቤህግ የቅጣት አስተያየታቸውን ሚያዚያ 17 ቀን 2008ዓ.ም ለፍርድቤቱ ያመለከቱ ሲሆን ፍረድቤቱ የግራ ቀኙን አይቶ ዛሬ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 የእስራት ፍርድ ስጥቷል፡፡
አቃቤህግ ተከሳሾች የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ስራ ላይ ውሎ በነበረበት ግዜም ጭምር ወንጀል መፈፀማቸውን ቀጥለውበት የነበረ መሆኑን ገልፆ ፍርድቤቱ ቅጣት ሲያስተላልፍ በተሻሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ እንዲያደርግ ጠይቆ የነበረ ቢሆንም ፍርድቤቱ የወንጀል ድርጊቱ የተፈፀመው በአመዛኙ የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ከመውጣቱ በፊት በመሆኑ እና በድርጊቱም የተጎዳ ሰውም ሆነ ንብረት ስለሌለ የአቃቤውን ጥያቄ አልተቀበለም፡፡
ተከሳሾች ሲያደርጉት የነበረው እንቅስቃሴ በሰው ህይወት፣ንብረት እና አጠቃላይ በሀገር ደህንነት ላይ ሊያስከትል ከሚችለው ችግር አንፃር በመመዘን የተከሳሾቹን የወንጀል አፈፃፀም በከባድ በማለት ፍርድቤቱ መድቦ እንዲቀጡ አቃቤህግ የጠየቀውን ውድቅ ያደረገው ፍርድቤቱ ተከሳሾች የወንጀል ተግባሩን የፈፀሙት ቡድን መስርተው በስምምነት በመሆኑ እንደማክበጃ የወ/ህ/ቁ 84/1/መ/ እንዲያዝለት አቃቤህግ ያመለከተውን ተቀብሎታል፡፡
ተከሳሾች በበኩላቸው ከዚህ በፊት በምንም አይነት ወንጀል ተከሰው የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዳልተላለፈባቸው፣ሁሉም ተከሳሾች የቤተሰብ አስተዳዳሪ ሰለመሆናቸው ታሳቢ ተደርጎ ቅጣት እንዲቀልላቸው ያመለከቱተን ፍርድቤቱ የተቀበለ ሲሆን አንደኛ ተከሳሽ በጋምቤላ ክልል ከ1978 እስከ 1992 ለ13 ዓመታት በጤና ቢሮ የተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች እስከ ክልሉ ፕሬዝዳንትነት የክልሉን ህዝብና የፌደራሉን መንግስት ያገለገሉ መሆኑን ጠቅሰው እንደ ቅጣት ማቅለያ እንዲያዝላቸው ያመለከቱትን ግን ፍርድቤቱ አልተቀበለውም፡፡
በዚህም አንደኛ ተከሳሽ ኦኬሎ አኳይ የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን እና የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል በቡድን ሆኖ የአመራር ሚናን በኃላፊነት በመምራታቸው በዘጠኝ አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድቤቱ ወሰኗል፡፡
ሁለተኛ ተከሳሽ ዴቪድ ኡጁሉ የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል እና የውጪ ጉዳይ ኃላፊ በመሆን የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ቡድኑን በአመራር በማገልገላቸው በተመሳሳይ በዘጠኝ አመት ፅኑ እስራት ቀጥቷል፡፡
ከሶስተኛ እስከ ሰባተኛ ያሉ ተከሳሾች (ኡቻን ኦፔይ፣ ኡማን ኝክየው፣ ኡጁሉ ቻም፣ አታካ ኡዋር እና ኡባንግ ኡመድ ) በጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን የተለያዩ ተሳትፎዎችን በማድረጋቸው ሁሉም ተከሳሾች በሰባት አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድቤቱ ወሰኗል፡፡
በሰኔ ወር 2006ዓ.ም በፌደራል አቃቤህግ ክስ የተመሰረተባቸው እነ ኦኬሎ አኳይ ለሁለት አመት ከማንኛውም ህዝባዊ መብቶቻቸው እንዲታገዱ ፍርድቤቱ አዟል፡፡
ምንጭ፡-http://ehrp.org