(አዲስ ሚዲያ) ለረጀም ጊዜ የኢትዮጵያ ረጅም ርቀት ሩጫ ውድድር አሰልጣኝ የነበሩት ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ69 ዓመታቸው ትናንት ሰኞ ግንቦት 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ዶ/ር ወልደመስቀል ኢትዮጵያ ከነ አበበ ቢቂላ፣ ማሞ ወልዴ እና ምሩፅ ይፍጠር በኋላ በጋራም ሆነ በግል በሚገኙ አትሌቶች የድል ውጤት ዋነኛ ተጠቃሽ አሰልጣኝ ናቸው፡፡
በተለይም አትሌት ኮሎኔል ደራርቱ ቱሉ፣ አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ፣ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ አትሌት ጠሩነሽ ዲባባ፣ አትሌት ብርሃኔ አደሬ፣ አትሌት ጌጤ ዋሚ፣ አትሌት ወርቁ ቢቂላ፣ አትሌት ፊጣ ባይሳ፣ አትሌት አሰፋ መዝገቡ፣ አትሌት ስልሺ ስህን፣…የመሳሰሉ ስመጥር አትሌቶችን ያፈሩ በማፍራት በርካታ የወርቅ፣ የብር እና የነሐስ ሜዳልያ ሽልማቶችን ከአትሌቶቹ በተጨማሪ ሀገሪቷም እንድታገኝ ያስቻሉ ታላቅ ሰው ነበሩ፡፡
ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ ከ1964 ዓ.ም. ጀምሮ ለ30 ዓመታት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ የረጅም ርቀት አሰልጣኝነት ላበረከቱት አስተዋፅዖ በሀገሪቱ መንግሥትም ሆነ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የተሰጣቸው ዕውቅናም ሆነ ሽልማት ባይኖርም፤ የዓለም አቀፍ አትሌቲክ ማኀበር (IAAF) በ1998 ዓ.ም. (እ.አ.አ በ2006) ምርጥ አሰልጣኝ በሚል ተሸላሚ እንደነበሩ አይዘነጋም፡፡