(አዲስ ሚዲያ)እሁድ ሰኔ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በኢትዮጵያ እና በኤርትራ ድንበር መካከል ዳግም ግጭት ተቀሰቀሰ፡፡ ግጭቱ የተቀሰቀሰው በሁለቱም ሀገራት ድንበር አካባቢ በሚገኘው ፆረና ግንባር ሲሆን፤ ዘግይተውም ቢሆን ሁለቱም ሀገራት ግጭት መኖሩን በሰጡት መግለጫ አረጋግጠዋል፡፡ ግጭቱን በተመለከተ ቀደም ብሎ መግለጫ የሰጠው የኤርትራ መንግሥት ማስታወቂያ ሚኒስቴር “የህወሓት አገዛዝ በፆረና ማዕከላዊ ግንባር ጥቃት ሰንዝሮብኛል፣ አጠቃላይ ዝርዝር መረጃውን በሚመለከት ይፋ እናደርጋለን” ሲል መግለጫ ሰጥቷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት በበኩሉ “የኤርትራ መንግሥት በፆረና በኩል ትንኮሳ ሲጀምር የአፀፋ ርምጃ ወስደናል፣ ትንኮሳውንም ካላቆመ ተመጣጣኝ ርምጃ መውሰዱን እንቀጥላለን” ማለቱን አስታውቋል፡፡
ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ለእሁዱ ግጭት መከሰት ዋነኛ ምክንያት እና በሁለቱም በኩል ስለደረሰ ጉዳት መንግሥታዊ ይፋ የሆነ ማብራሪም ሆነ መግለጫ የለም፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ኤርትራ ፕሬስ ከሆነ፤ የኤርትራ ሰራዊት ሰኞ ጠዋት በወሰደው የመልሶ ማጥቃት ከባድ ውጊያ በደቡብ ፆረና ኩዱ ሃዋይ ወታየኢትዮጵን ድንበር ጥሶ በመግባት 52 ወታደሮች መማረካቸውን ዘግቧል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው በተከሰተው ግጭት የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ ወደፊት እንደሚገልፁ ለዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን አስታውቀዋል፡፡ ሚኒስትሩ በጉዳዩ ዙሪያ ዛሬ ለሀገር ውስጥ ጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ “የአገር መከላከያ ሰራዊት የወቅቱን ትንኮሳ ታሳቢ በማድረግ ባለፉት ሁለት ቀናት የኤርትራን መንግስት ለታላቅ ኪሳራ የሚዳርግና ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ላደረገው ትንኮሳ መልስ የሚሆን እርምጃ ወስዷል” ብለዋል።
በሁለቱም ሀገራት ድንበር መካከል የተከሰተውም ግጭት ትናንት ከሰዓት በኋላ መቆሙን የኢትዮጵያ መንግሥት እንዳስታወቀ ሀገር ሸገር ኤፍ ኤም በቀትር ዜና እወጃው ዘግቧል፡፡
በተለይ በሁለቱም ሀገራት መካከል በ1990/91ዓ.ም. ከተደረገው ጦርነት ጀምሮ በድንበር አካባቢ “ሰላምና ጦርነት አልባ” ስጋት እንዳንዣበበ ይታወቃል፡፡