ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከህዳር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል በተካሄዱ የተቃውሞ ሰልፎች የኢትዮጵያ መንግስት የጸጥታ ሀይሎች ከ400 በላይ የሚሆኑ ሰልፈኞችን የገደሉ ሲሆን ከአስር ሺህ በላይ የሚቆጠሩትን ደግሞ ማሰራቸውን አስታውቋል፡፡ የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ “የኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸሙ ግድያዎችን፣ እስራቶችንና ሌሎች የመብት ጥሰቶች በአስቸኳይ ተአማኒነት ያለውና ገለልተኛ የሆነ ማጣሪያ እንዲካሄድ ድጋፍ ማድረግ አለበት።” ሲል ባለ 61 ገፅ ሪፖርት ይፋ አድርጓል፡፡
ድርጅቱ ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው ባለ 61 ገጽ ሪፖርት “ጭካኔ የተሞላበት አፈና’ – የግድያ እና የእስራት ምላሽ፤ ለኢትዮጵያ የኦሮሞ ተቃውሞ” የሚል ነበር፡፡ መንግሥትም በነበረው ተቃውሞ ያልተመጣጠነ ርምጃ መውሰዱን በመግለፅ ድርጊቱን አውግዟል፡፡ ሪፖርቱ በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ እንዲሁም ሀሳባቸውን በነጻነት በሚገልጹ ዜጎች ላይ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች የተወሰደውን እርምጃ አስመልክቶ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን፣ ከ125 በላይ የሚሆኑ የተቃውሞ ሰልፎች ተሳታፊዎችን፣ ጉዳዩን በአንክሮ ሲከታተሉ የቆዩ ግለሰቦችን፣ በተለያዩ ጊዜያት የመብት ጥሰት የተካሄደባቸውና ጉዳት የደረሰባቸውን ግለሰቦች ያካተተ ቃለ መጠይቅ ማድረጉንም አስታውቋል፡፡
በመንግሥት የተቋቋም የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮምሽን ይህንን የኦሮሚያ ክልል ተቋውሞ ተከትሎ በተወሰደ ርምጃ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 173 ብቻ መሆናቸውን እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃም “ተገቢና ተመጣጣኝ” ነው ሲሉ ኮሚሽነሩ ዶ/ር አዲሱ ገብረእግዚአብሔር ሰኔ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. “ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት” እና ለጋዜጠኞች ገልፀዋል፡፡ ኮሚሽነሩ ተገቢና ተመጣጣኝ ያሉት ርምጃ የተወሰደው በመከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ እና በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል መሆኑንም ለጋዜጠኞች ጠቁመዋል፡፡
መንግሥታዊ ያልሆነው ሀገር በቀል የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ፤ በኦሮሚያ ክልል በነበረው ተቃውሞ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃ ተገቢና ተመጣጣኝ እንዳልሆነ ቀደም ሲል ይፋ ባደረገው ዝርዝር ሪፖርት ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በነበረውን ተቃውሞ የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ፤ ሀገር በቀል የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ባለፈው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም በመግለፅ ሪፖርቱን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡
ሙሉውን የሂውማን ራይትስ ዎች ሪፖርት እዚህ https://www.hrw.org/news/2016/06/15/ethiopia-protest-crackdown-killed-hundreds ያገኙታል፡፡