ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም ላቀረበው የክስ መቃወሚያ አቃቤ ህግ መልስ ሰጥቷል፡፡
የፌደራል አቃቤ ህግ ሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት ቀርቦ በተከሳሹ የክስ መቃወሚያ ላይ ለተነሱ ነጥቦች በጽሁፍ መልሱን ለችሎቱ አስገብቷል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው አቃቤ ህግ ያቀረበበት ክስ ‹‹በማናቸውም መልኩ በሽብር ተግባር መሳተፍ›› የሚለው፣ አንድ ሽብርተኛ ተብሎ የተሰየመን ድርጅት ስም መጥራት፣ የሽብር ድርጅቱ በሚጠቀምበት ሚዲያ መጠቀም ወይም የሽብር ድርጅት አባል ነው የተባለን ሰው ለሽብር ድርጅቱ አንዳችም ፋይዳ በሌለው ነገር ላይ ማነጋገር ሁሉ ይጨምራል በሚል ተለጥጦ መቅረብ እንደሌለበት ላቀረበው መቃወሚያ፣ አቃቤ ህግ ድንጋጌውና የወንጀል ዝርዝሩ በሚመጣጠን መልኩ ክሱ ቀርቧል ሲል መልስ ሰጥቷል፡፡ ስለሆነም መቃወሚያው በአግባቡ ያልቀረበ በመሆኑ ውድቅ እንዲደረግለት ጠይቋል፡፡
ተከሳሽ አቃቤ ህግ በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ስለነበሩ ክስተቶች የሽብር ድርጅት አመራር ናቸው ላላቸው ሰዎች መረጃ ማስተላለፍን በሽብር ድርጅቱ ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ እንደሆነ አድርጎ ማቅረቡ ስህተት ብቻ ሳይሆን ከህጉ አላማም በእጅጉ የራቀ ነው፣ የህጋዊነት መርህንም የተከተለ አይደለም በሚል ላቀረበው መቃወሚያ፣ አቃቤ ህግ ክሱ የህጋዊነትን መርህ ባከበረ መልኩ የቀረበ መሆኑን በመጥቀስ የወንጀል ድርጊቱ በማስረጃ የሚረጋገጥ ይሆናል በማለት መቃወሚያው ውድቅ ይደረግልኝ ሲል አመልክቷል፡፡
አንድ ድርጊት ወንጀል ነው አይደለም የሚለው ፍ/ቤት ማስረጃ ከሰማ በኋላ የሚወሰን ስለመሆኑ ጥር 27 ቀን 2007 ዓ.ም ፌደራል ሰበር ሰሚ ችሎት አስገዳጅ ውሳኔ መስጠቱን በማስታወስ የወንጀል ድርጊቱ ላይ የተነሳው መቃወሚያ ከማስረጃ መሰማት በፊት ሊነሳ የማይገባው ነጥብ ስለሆነ ውድቅ ይደረግልኝ ብሏል፡፡ አቃቤ ህግ ያቀረበው ክስ የወ/መ/ሥ/ሥ/ሕጉ አንቀጽ 111 እና 112 መሰረት አድርጎ ተሟልቶ መቅረቡንም በመልሱ ላይ ገልጹዋል፡፡
ተከሳሹ ከሽብር ቡድኑ ተልዕኮ እንደተቀበለ ከመጠቀሱ በቀር ተልዕኮው ምን እንደሆነ፣ መቼ፣ ከማን እና በምን አይነት መንገድ ተልዕኮውን እንደተቀበለ ከሳሽ ግልጽ አላደረገም በሚል ለጠቀሰው መቃወሚያ፣ አቃቤ ህግ ‹‹ተልዕኮ መቀበል ሲባል የሽብር ቡድኑ አላማን በመቀበል የድርጅቱን አላማ በማራመድ በመንግስት ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ህብረተሰቡን ለማስፈራራትና የሀገሪቱን መሰረታዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ህገ-መንግስታዊ፣ ኢኮኖሚያዊ…ተቋማትን ለማናጋትና ለማፈራረስ በሚንቀሳቀስ የሽብር ቡድን ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ›› እንደሆነ ገልጾ የመቃወሚያው መቅረብ የህግ መሰረት የሌለው በመሆኑ ውድቅ ይደረግልኝ ሲል አመልክቷል፡፡
አቃቤ ህግ በአጠቃላይ ያቀረብኩት ክስ ህጉን መሰረት ያደረገና የክስ ዝረዝርና የህግ ድንጋጌውን ባጣጣመና በተገቢው መንገድ የቀረበ ስለሆነ በከሳሽ በኩል የቀረበው መቃወሚያ ውድቅ ተደርጎ ክርክራችንን እንድንቀጥል ሲል ጠይቋል፡፡
ችሎቱ ተከሳሹ ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ላይ አቃቤ ህግ የሰጠውን መልስ አገናዝቦ ብይን ለመስጠት ለሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በዛሬው የችሎት ውሎ 14ኛ ወንጀል ችሎት ቦታው በሙሉ በተከሳሾች ተይዟል በሚል ችሎቱን ለመታደም የቻለ የለም፡፡
ምንጭ፡- EHRP