በአዲስ አበባ በመንግሥት እና በህዝብ መካከል በተፈጠረ አለመግባባት የአዲስ አበባ ፖሊሶች ተገደሉ!

(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፈለ ከተማ ወረዳ 1 በተለምዶ ፉሪ ሐና ማርያም ቀርሳ ኮንቱማ እና ማንጎ ሰፈር በሚባል ስፍራ ትናንት ሰኔ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. እና ዛሬ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በነዋሪውና በከተማ አስተዳደሩ መካከል በተፈጠረ ግጭት ከ4 ያላነሱ የአዲስ አበባ ፖሊሶች፣ 1 አፍራሽ ግብረ ኃይል እና 1 የአካባቢው የወረዳ ባለስልጣን መገደላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ እንደ አካባቢው የዓይን እማኞች ገለፃ ከሆነ፤ ከነዋሪዎችም በርካታ ሰዎች በፖሊስ በተተኮሰ ጥይት መቁሰላቸውን እና የህክምና እርዳታም እንዳያገኙ መደረጋቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ በተፈጠረው ግጭት የሟቾች ቁጥር ከተጠቀሰው በላይ ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡ መንግሥት በበኩሉ ዛሬ በተፈጠረው ግጭት ሁለት ፖሊስ እና የአካባቢው የወረዳ ባለስልጣን መገደላቸውን አስታውቋል፡፡

Dead police at AA hana mariam lafto area

የግጭቱ ዋነኛ ምክንያት መንግሥት በአካባቢው ያሉ 30 ሺህ ያህል ነዋሪዎች ከመንግሥት እውቅና ውጭ በህገ ወጥ መንገድ ቤት ሰርተው እየኖሩ ያሉ ሰዎች ቤታቸውን አፍርሰው ከአካባቢው መነሳት አለባቸው የሚል ውሳኔን ተከትሎ፤መንግሥትም ቤቶቹን ለማፍረስ የቤት አፍራሽ ግብረ ኃይል፣ የአዲስ አበባ ፖሊሶች፣ አራት ሲቪለ የለበሱ ማንነታቸው ያልታወቁ ሰዎች፣ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ የመብራት ኃይል ሰራተኞች እና ሁለት የአካባው የወረዳ አመራር ወደስፍራው ልኮ እንደነበር ታውቋል፡፡

የቤታቸውን መፍረስ በመቃወም የአካባቢው ሴቶችና ህፃናት ወደ አዲስ አበባ ሴቶችና ህፃናት ቢሮ ቅሬታ ለማቅረብ ቢሄዱም ሰሚ ሳያገኙ ቀርተዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ሐና ማርያም አካባቢ የሚገኘው የወረዳው አስተዳደር የአካባቢውን ነዋሪ በቤት መፍረሱ ጉዳይ ኑና እንነጋገር በሚል ከጠራ በኋላ፤ በጎን ወደነዋሪዎቹ አካባቢ አፍራሽ ግብረ ኃይል መላኩ ነዋሪውን ይበልጥ እንዳበሳጨውና ለህይወት መጥፋት ዋናው መንስኤ እንደሆነ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡

ቤቶቻቸው በኃይል እንዲፈርስ ከተደሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ምንም ዓይነት ካሳ እና ምትክ ቤትም ሆነ ቦታ በመንግሥት እንዳልተሰጣቸው የጠገለፀ ሲሆን፤ እንዲፈርሱ በተወሰነው የመንደሩ ነዋሪዎች በርካታ አዛውንት፣ ህፃናት፣ ነፍሰጡር እናቶች እንደሚገኙ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ወቅቱ ከፍተኛ ዝናብ የሚዘንብበት ክረምት በመሆኑ፤ ነዋሪዎች ቤቶቻቸው ያለምንም ምትክ ቤትና ካሳ ቤቶቻቸው የሚፈርሱ ከሆነ ህፃናትና ነፍሰጡር እናቶችን ጨምሮ ሁሉም ለጎዳና ህይወት እንደሚዳረጉ እየተናገሩ ይገኛል፡፡ ይሁን እንጂ ከመንግሥት በኩል ስለምትክ ቤትና ቦታም ሆነ ካሳን በሚመለከት እስካሁን የተባለ ነገር የለም፡፡ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በአካባቢው አሁንም ውጥረት እንደነገሰ ነው፡፡

ባለፈው ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በተመሳሳይ መልኩ በቦሌ ልፍለከ ከተማ ወረዳ 12 ልዩ ስሙ ወረገኑ በሚባል ስፍራ 20 ሺህ ያህል ነዋሪዎች ያሉበትን ቤት፤ መንግሥት ህገወጥ ነው በሚል ለማፍረስ በመንቀሳቀሱ በተፈጠረ አለመግባባት የሰው ህይወት መጥፋት የአካል ጉዳት ማስከተሉ አይዘነጋም፡፡

Leave a comment