(አዲስ ሚዲያ) የቀድሞው የአንደነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው አቶ ሀብታሙ አያሌው የጤናው ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ በመድረሱ ተገቢውን ህክምና ማግኘት አለመቻሉ ታውቋል፡፡ ባለፈው ማክሰኞ ሰኔ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ህመሙ ይበልጥ ተባብሶ ራሱን በመሳቱ በአቅራቢያ ወደሚገኘው ዋሸንግተን ሆስፒታል ቢወሰድም ተገቢውን የህክምና ዕርዳታ ማግኘት ባለመቻሉ ወደ ቤተዛታ ሆስፒታል ቢወሰድም ተገቢውን የህክምና ርዳታ ባለማግኘቱ ወደ ካዲስኮ ሆስፒታል ተወስዶ በማስታገሻ ሆስፒታል ውስጥ አልጋ ይዞ እንዲቆይ ተደርጓል፡፡
አቶ ሀብታሙ የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል “ማዕከላዊ”ን ጨምሮ ለ18 ወራት ያህል በታሰረበት ባጋጠመው ህመም ምክንያት የህክምና ዕርዳታ ቢጠይቅም ከመንግሥት በጎ ምላሽ ባለመገኘቱ ከእስር በነፃ ከተለቀቀ በኋላ ህመሙ እንደተባባሰ ተጠቁሟል፡፡
አቶ ሀብታሙ በሀገር ውስጥ ባሉ የተለያዩ የህክምና ተቋማት ተገቢውን የህክምና ክትትል ለማድረግ ቢንቀሳቀስም ህመሙ ካለበት ከፍተኛ ደረጃ አንፃር አቅም ካለው ከሀገር ውጭ ሄዶ ቢታከም የተሻለ እንደሆነ ከዶክተሮቹ በተነገረው መሰረት በውጭ ሀገር ህክምና ማድረግ ቢፈልግም፤ የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከሀገር እንዳይወጣ በጣለው እግድ መሰረት ተገቢውን ህክምና ባለማግኘቱ ማክሰኞ ራሱን መቆጣጠር የማይችልበት ደረጃ ላይ መድረሱ ታውቋል፡፡ በአቃቤ ህግ ይግባኝ ምክንያት ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለው የፍርድ ቤት እግድ እንዲነሳ አቶ ሀብታሙ በጠበቃቸው አቶ አምሃ መኮንን አማካኝነት ፍርድ ቤቱን ቢጠይቅም እስካሁን ምላሽ እንዳልተገኘ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ኢትዮጵያውያን በማኀበራዊ ሚዲያ እና አምንስቲ ኢንተርናሽናል አቶ ሀብታሙ ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለበት እግድ እንዲነሳ እና ተጊቢውን የህክምና ዕርዳታ እንዲያገኝ ሊፈቀድ ይገባል ሲሉ ጥያቄ ያቀረቡ ሲሆን፤ የማኀበራዊ ሚዲያ ዘመቻው እስከነገ እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡ ይህ እስከ ተዘገበበት ድረስ አቶ ሀብታሙ ራሱን ስቶ በከፍተኛ ስቃይ ውስጥ በካዲስኮ ሆስፒታል ተኝቶ እስኪነቃ በሚል ከሚሰጠው ማስታገሻ በስተቀር ምንም ዓይነት መደበኛ የህክምና ዕርዳታ እንዳልጀመረ ታውቋል፡፡