በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ በተቀሰቀሰ ግጭት 4 ሰዎች ተገደሉ

(አዲስ ሚዲያ)በምስራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ ትናንት ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት በመንግሥት ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት የ9 ዓመት ህፃንን ጨምሮ 4 ያህል ነዋሪዎች በከተማው አስተዳደርና በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኘው የሐሮማያ ሆስፒታል በበኩሉ የተገደሉት ሰዎች ቁጥር 4 መሆኑን እና የቆሰሉ 3 ሰዎች በሆስፒታሉ የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ተጠቁሟል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት ከሆነ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 6 እንደሆነ እና በፅኑ የቆሰሉት ደግሞ 4 እንደነበሩ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡

Aweday firing

በዕለቱ የግጭቱ መነሻ እንደሆነ የተነገረው በአወዳይ ከተማ ውስጥ ያለ አንድ የሞባይል ስልክ መሸጫ ሱቅና አጠገቡ ያለው የፍራሽ መሸጫ ሱቅ ባልታወቀ ምክንያት በመቃጠላቸው የተነሣ የአከባቢው ህዝብ እሳቱን ለማጥፋት ጥረት ቢያደርግም ሊሳካ ባለመቻሉ በአከባቢው ያሉትን የባለሥልጣናት ለእርዳታ ቢማፀኑም ቆመው ከመሳቅ ባለፈ ምንም እርዳታ ባለማድረጋቸው የተበሳጩ ነዋሪዎች “ድሮም እናንተ የምታደርጉልን ነገር የለም” ስለዚህ ከዚህ ሂዱ ብለው በመናገራቸው የፀጥታ ኃይሎች በስልክ ወደ ቦታው መጠራታቸውንና ግጭቱ መከሰቱን የአካባቢውን ነዋሪ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የነጋዴዎቹን ሱቅ ቃጠሎ ተከትሎ በህዝቡና በመንግሥት በተለይም በአካባቢው አስተዳደር አካለትና የፀጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ አለመግባባት የአወዳይ ቀበሌ 02 ሊቀመንበር አቶ አብዲ ኢድሪስ በቃጠሎው ስፍራ የነበሩ ነዋሪዎች ላይ በከፈቱት ተኩስ የ9 እና የ13 ዓመት ህፃናት ቆሰሉ፡፡ በሊቀመንበሩ የቆሰሉ ህፃናትም ወደ አካባቢው የጤና ተቋም ቢወሰዱም ወዲያው ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች በቁጣና በጩኸት ወደቆሰሉ ህፃናት ሲመጡ የኦሮሚያ ልዩ ፖሊስ እና የፌደራል ፖሊስ በድንገት ወደስፍራው በመምጣት፣ አንድ የፌደራል ፖሊስ አባል ተኩስ ከፍቶ 3 ወጣቶች ወዲያው ሲገደሉ፤ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎችም በፅኑ መቁሰላቸውን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኝ ተናግረዋል፡፡

Aweday town protest

በመንግሥትና በህዝቡ መካከል በተፈጠረው ግጭት ምክንያት በአወዳይ የሐረር መንገድ ዝግ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ይሁን እንጂ በግጭቱ ዙሪያ እስካሁን ከመንግሥት አካል የተሰጠ መግለጫም ሆነ ማብራሪያ ማግኘት አልተቻለም፡፡

Leave a comment