*ጌታቸው ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደርጓል
ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የእምነት ክህደት ቃሉን ለፍርድ ቤት ሰጥቷል፡፡
አርብ ሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበው ጋዜጠኛ ጌታቸው ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ መሆኑን ተከትሎ የእምነት ክህደት ቃሉን እንዲሰጥ በችሎቱ ተጠይቆ ‹‹የቀረበብኝን የወንጀል ድርጊት አልፈጸምኩም፤ ጥፋተኛም አይደለሁም›› ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡
መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው ተከሳሹ ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያን መርምሮ ብይን ለመስጠት ሲሆን፣ ጉዳዩን የሚያየው 14ኛ ወንጀል ችሎት የተከሳሹን መቃወሚያ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ አድርጎታል፡፡ ችሎቱ የመቃወሚያ ብይኑን በንባብ ከማሰማት ይልቅ በጥቅሉ “የቀረበውን መቃወሚያ ውድቅ አድርገነዋል” ሲል ለተከሳሹ ገልጹዋል፡፡
”በአጭሩ የክስ አቀራረቡ ከተጠቀሰው የወንጀሉ ክፍል አለመጣጣምን በተመለከተ የቀረበው መቃወሚያ አልተቀበልነውም፤ ዝርዘሩን ማስረጃ ስንመዝን እናየዋለን፡፡ የቀረበው ክስ ግልጽ አይደለም የተባለውን በተመለከተም፣ ክሱን ስንመለከተው በተብራራ መልኩ የቀረበ መሆኑን ስለተገነዘብን ውድቅ አድርገነዋል” በማለት የመቃወሚያው ውድቅ መሆንን ችሎቱ በቃል ለተከሳሹ አስረድቷል፡፡
ችሎቱ ተከሳሹ የእምነት ክህደት ቃሉን ሲሰጥ ወንጀሉን አልፈጸምኩም፣ ጥፋተኛም አይደለሁም ማለቱን ተከትሎ የአቃቤ ህግን አስተያየት የጠየቀ ሲሆን፣ አቃቤ ህጉ በበኩሉ ከክስ ማመልከቻ ጋር ያያያዘው የሰነድ ማስረጃ ተመርምሮ ብይን እንዲሰጥለት አመልክቷል፡፡
ፍርድ ቤቱም የሰነድ ማስረጃውን መርምሮ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ ከሳሽ ያቀረበበት የሰው ማስረጃ እንደሌለ በችሎቱ ተገልጹዋል፡፡
ምንጭ፡- EHRP