ከመጋቢት 2007 ዓ.ም ጀምሮ የዋስ መብት በፍርድቤት ተከልክለው በእስር የሚገኙት እነ ኦሞት አግዋ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የህግ አማካሪና ጠበቃቸው አመሃ መኮንን በህመም ምክንያት ችሎት ባለመገኘታቸው መዘገቡ የአቃቤ ህግ ምስክር ለመስማት ብቻ ለዘጠነኛ ጊዜ ተቀጥሯል፡፡
አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ ጠበቃችን አመሃ መኮንን ታመው ሆስፒታል የተኙ ስለሆነ ያለእርሳቸው ውክልና ምስክር እንዳይሰማብን ፍርድቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን ሲሉ ሶስቱንም ተከሳሾች ወክለው ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡
በዕለቱ ችሎት አቃቤ ህግ አሉኝ ካላቸው ሰባት ምስክሮች መካከል ሶስቱ በችሎቱ ምስክርነታቸውን ለመስጠት ቀርበው ነበር፡፡
ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለአቃቤ ህግ ምስክር ለመሆን የመጡት ቄስ ሽብሩ ኦጅራ በተደጋጋሚ መጥተው ሳይመሰክሩ ተመልሰውብኛል ስለዚህ እንዲመሰክሩ ይደረግልኝ ብሎ ለተከራከረው አቃቤህግ፣ ዳኛ ታረቀኝ አማረ የስነስርዓት ህጉ ተከሳሾች ያለጠበቃቸው ውክልና እንዲከራከሩ አይፈቅድም በሚል ጥያቄውን ውድቅ አድርገውታል፡፡
የአቃቤ ህግ ምስክር ቄስ ሽብሩ ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለምስክርነት ለመጡበት የሁለት ቀን ትራንስፖርት እና አበል እንዲከፈላቸው እንዲሁም ዛሬ የቀረቡ ምስክሮች ያለምንም የፍርድቤት መጥሪያ ሌሎች ተጨማሪ የአቃቤህግ ምስክሮች በጠቅላላ በቀጣይ ቀጠሮ ነሐሴ 9 ቀን 2008 ዓ.ም እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ. ም ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) የክስ መዘገብ ላይ አቃቤ ህግ ምስክሮችን ማሰማት የጀመረው መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡
ምንጭ፡- EHRP