የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አቶ ዮናታን ተስፋዬን ፍር ቤት እንዳልቀረበ ተገለፀ

በኦሮምያ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለማስቀጠል ፌስቡክ ላይ በመጻፍ ተንቀሳቅሰሃል በሚል በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ የቀረበበት የሰማያዊ ፓርቲ የቀድሞው ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ  ሐምሌ 20 ቀን 2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀጠሮ የነበረው ቢሆንም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ተከሳሹን አላቀረበውም፡፡

Yonatan Tesfaye

የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ለዛሬ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለማድመጥ ቀጠሮ ይዞ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ተከሳሽ በእስር የሚገኝበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ሳያቀርበው ቀርቷል፡፡ ተከሳሹን ለምን እንዳላቀረበ የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ተወካይ እንዲያስረዳ ተጠይቆ፣ የዕለቱ ጉዳይ አስፈጻሚ ሳሙኤል ደሚ ‹‹ተከሳሹ ታሞ አላቀረብነውም›› የሚል መልስ በቃል ሰጥቷል፡፡

ከሳሽ የፌደራል አቃቤ ህግ ሁለት ምስክሮቹን ለማሰማት አቅርቦ ነበር፡፡ ሆኖም ተከሳሹ ባለመቅረቡ ሁለቱ ምስክሮች አቶ አብርሃም ወልዴ እና አቶ መኮንን በላይ በቀጣይ ቀጠሮ ተጨማሪ መጥሪያ ሳያስፈልጋቸው ቀርበው እንዲመሰክሩ በዳኞች ተነግሯቸው ተመልሰዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ሁለቱን ምስክሮች ለመስማት ለሐምሌ 22 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል አቶ ዮናታን ተስፋዬ በጨለማ ቤት ታስሮ እንደሚገኝና በእስር ቤት ሰብዓዊ መብት ጥሰት እየተፈጸመበት እንዳለ ጠቅሶ አያያዙ እንዲሻሻልለት ሰኔ 14 ቀን 2008 ዓ.ም አቤቱታ ማስገባቱ ይታወሳል፡፡

ማረሚያ ቤት ለዚህ አቤቱታ ሐምሌ 14 ቀን 2008 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ መልስ ሰጥቷል፡፡ ችሎት ሳይሰየም ጉዳዩን በቢሮ የተመለከቱት ዳኞች የተሰጠውን የጽሁፍ መልስ ለተከሳሽ ጠበቃ በንባብ አሰምተዋል፡፡ በዚህም ማረሚያ ቤቱ ጨለማ ክፍል እንደሌለው፣ አቶ ዮናታን ከሌሎች እስረኞች በተለየ እንዳልተያዘ በመግለጽ ተከሳሹ ያቀረበው አቤቱታ ከእውነት የራቀና ስም ማጥፋት ስለሆነ ፍርድ ቤቱ ማስጠንቀቂያ ይስጥልኝ የሚል መልስ እንደሰጠ የጽሁፍ መልሱ በንባብ ሲሰማ ለመረዳት ተችሏል፡፡

የተከሳሽ ጠበቃ በበኩላቸው የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር የሰጠው መልስ ክህደት መሆኑን በመግለጽ፣ ደንበኛቸው ችሎት ያልቀረበው በማመልከቻው ላይ እንደገለጸው የመብት ጥሰት እየተፈጸመበት መሆኑን በመቃወም የርሃብ አድማ ላይ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ደንበኛዬ በማመልከቻው የገለጸው የመብት ጥሰት እንደተፈጸመበትና እየተፈጸመበት ስለመሆኑ ማስረጃ አለን›› ብለዋል የተከሳሽ ጠበቃ፡፡ ፍርድ ቤቱ በበኩሉ ጉዳዩን ተከሳሹ በአካል ሲቀርብ እንደሚያየው በመግለጽ ለሐምሌ 22 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ ዛሬ ችሎት ያልቀረበው ለሳምንት የዘለቀ የርሃብ አድማ ላይ በመሰንበቱ ሰውነቱ ተዳክሞ ሊሆን እንደሚችል ከቤተሰቦቹ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ተከሳሹ ባለፈው ቀጠሮ የእምነት ክህደት ቃሉን በሰጠበት ወቅት፣ ‹‹ክሱ በቀረበበት መንገድ የተገለጸውን የሽብር ተግባር አልፈጸምኩም፡፡ ሀሳቤን በነጻነት የመግለጽ መብቴን ተጠቅሜ ግን ጽፌያለሁ፡፡ በመሆኑም የሽብር ተግባር አልፈጸምኩም፤ ጥፋተኛ አይደለሁም›› ማለቱ ይታወሳል፡፡
ምንጭ፡- ኢሰመፕ

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: