የሪዮ ኦሎምፒክ እና የኢትዮጵያ መንግሥት ገመና

ብስራት ወልደሚካኤል

ኢትዮጵያ ከሐምሌ 29 እስከ ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በተካሄደው የ2016ቱ የብራዚሉ የበጋ ሪዮ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ 35 ስፖርተኞችን በ3 ዘርፍ በማሳተፍ 8 ሜዳሊያ በማግኘት ከዓለም ተወዳዳሪዎች 44ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች፡፡ በበርካታ ዓለም አቀፍና የኦሎምፒክ ውድድሮች ኢትዮጵያ በምታገኛቸው ድሎች ትበልጣት የነበረችውና በአፍሪካ የቅርብ ተቀናቃኟ ኬንያ በበኩሏ 13 ሜዳሊያ በማግኘት 15ኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች፡፡

ኢትዮጵያ ለ13ኛ ጊዜ የበጋ በሪዮ ኦሎምፒክ ውድድር የተሳተፈችው በሶስት የውድድር ዘርፍ በተለይም በአትሌቲክስ ሩጫ፣ ዋና እና ብስክሌት ውድድር ሲሆን፤ ሜዳሊያ ያገኘችው በሩጫው የአትሌትክስ ዘርፍ ብቻ ነው፡፡ በዚህም 1 ወርቅ፣ 2 ብር እና 5 ነሐስ ያገኘች ሲሆን በአጠቃላይ 8 ሜዳሊያ አግኝታ ተመልሳለች፡፡ ባለፈው የለንደኑ 2012ቱ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ በ2 ስፖርት ዘርፍ 35 ተወዳዳሪዎችን በማሰለፍ 3 ወርቅ፣ 2 ብር እና 2 ነሐስ በአጠቃላይ 7 ሜዳሊያ በማግኘት በዓለም 23ኛ ደረጃን በመያዝ ያጠናቀቀች ሲሆን፤ በቤጂንጉ የ2008 ኦሎምፒክ በ1 ስፖርት ዘርፍ 27 ተወዳዳሪዎችን በማሰለፍ 4 ወርቅ፣ 1 ብር እና 2 ነሐስ አጠቃላይ 7 ሜዳሊያ በማግኘት 18ኛ ደረጃን ይዛ ነበር ያጠናቀቀችው፡፡ ይህም የኢትዮጵያ የኦሎምፒክ ውድድር፣ ተሳትፎ፣ ብቃት እና ውጤት ከጊዜ ወደ ጊዜ እጅግ እየቀነስ መሄዱን ቢያሳይም፤ በተለይ በአትሌቲክስና በሌሎች ፌዴሬሽኞች እንዲሁም በኦሎምፒክ ኮሚቴና በስፖርት ፌዴሬሽን በኩል ከመገናኛ ብዙኃኝ ፍጆታ ባለፈ ለስፖርቱ መሻሻል ትኩረት እንዳልተሰጠው ያሳያል፡፡

ኬንያ በ2012 የለንደኑ ኦሎምፒክ በ4 ስፖርት ዘርፍ 47 ተወዳዳሪዎችን አሳትፋ 2 ወርቅ፣ 4 ብር እና 6 ነሐስ በአጠቃላይ 12 ሜዳሊያ በማግኘት ከዓለም 28ኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀች ሲሆን፤ በ2008ቱ የቤጂንግ ኦሎምፒክ በ5 ስፖርት ዘርፍ 48 ተወዳዳሪዎችን በማሳተፍ 6 ወርቅ፣ 4 ብር እና 4 ነሐስ በአጠቃላይ 14 ሜዳሊያ 13ኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋይታወሳል፡፡ በርግጥ አብዛኞች የኢትዮጵያ ድሎች በአትሌቶች የግል ጥረት እንጂ በፌዴሬሽነች ስራ ጥረት እንዳልሆነ በተደጋጋሚ ቅሬታን መፍጠሩ የሚታወቅ ሲሆን፤ በሪዮ ኦሎምፒክም በተለይ በስመ ጥር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ሳይቀር ባልተለመደ መልኩ ከፍተኛ ተቃውሞና ቅሬታ መሰማቱ ይታወሳል፡፡

ኢትዮጵያ በ3 የውድድር መስክ በአጠቃላይ 38 ተወዳዳሪዎችን ለኦሎምፒክ ውድድሩ ብታስመዘግብም፤ እስካሁን ለምን እንደሆነ በይፋ የታወቀ ነገር ባይኖርም ውድድሩ ላይ ለመሳተፍ የጠጓዙት ግን 35 ተወዳዳሪዎች ብቻ ነበሩ፡፡ ተወዳዳሪዎችን አስቀርቶ በምትካቸው ከስፖርቱ ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸውን ልዑካን ይዞ መሄድ እና ስፖርቱን በፖለቲካዊ ዝምድና እና ማዕቀፍ ውስጥ መውደቁ አዲስ ባይሆንም፤ የሪዮ ኦሎምፒክ በሀገር ቤት የተገደበውን ፖለቲካዊ ፈር የለቀቀ ሙስና ለአደባባይ የበቃበት ክስተት አሳዛኝ ትዝታን አስፍሮ አልፏል፡፡ ይህ ክስተት ምንም እንኳ በሪዮ ኦሎምፒክ አዲስ ባይሆንም ከምን ጊዜውም ይበልጥ በተለይ ገዥውን ስርዓት በዓለም አደባባይ ያጋለጠ ነበር፡፡

የሪዮ ኦሎምፒክ ውድድር ውጤት ለኢትዮጵያ አስደሳች ባይሆንም፤ በዓለም የኦሎምፒክ መድረክ አሳዛኝ፣ አስደሳችና አሳፋሪ አዳዲስ ክስተቶች በኢትዮጵያውያን ተወዳዳሪዎች ለዓለም አደባባይ በቅቷል፡፡ በተለይ ስፖርታዊ ቅርፅም ሆነ ብቃት የሌለው ሮቤል ኪሮስ፣ አባቱ የውሃ ዋና ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት በመሆናቸው፣ የኦሎምፒክ ኮሚቴው ፕሬዘዳንት አቶ ብርሃነ ኪዳነማርያምና የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ ወ/ሮ ዳግማዊት ግርማይ አማካኝነት ብቃት ያላቸውን ተወዳዳሪዎችና የዋና አሰልጣኑ አበበ ቢቂላን ሀገር ቤት ጥለው ባላቸው የስጋና ፖለቲካዊ ዝምድና ብቻ በዓለም መድረክ ሀገርን ወክሎ እንዲወዳደር በማድረግ ሀገሪቱንም ልጁንም የዓለም መሳቂያ ማድረግ ችለዋል፡፡ በአትሌቲክ ፌሬሽንም ተመሳሳይ ቅሬታ ያለ ሲሆን፤ በተለይ የማራቶን አሰልጣኙ ሐጂ አዲሎ በጀት የለንም በሚል ከሪዮ ኦሎምፒክ እንዲቀሩ ተደርጉ፤ ከስፖርቱ ጋ ምንም ግንኙነት የሌላቸው እንደነ ሚሚ ስብሃቱ ያሉ የስርዓቱ ደጋፊ ሰዎች በኦሎምፒክ ኮሚቴ ወጪ እንዲጓዙ መደረጉም ታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ አሰልጣኙ ሐጂ አዲሎ አትሌቶቹ በውድድሩ ውጤታማ ይሆኑ ዘንድ ለማገዝ በራሱ ሙሉ ወጪ ብራዚል ሪዮ ኦሎምፒክ እንደሄደ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተለይ ሮቤል ኪሮስን የተለያዩ የስፖርት ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃንም ስፖርታዊ ብቃትና ቅርፅ አልባ መሆኑን በመታዘብ ሮቤል ዓሳ ነባሪው የሚል ስም በመስጠት ግርምታቸውን ለዓለም ህዝብ አሰራጭተው ነበር፡፡ በተለይ በሀገር ቤት በዋና ውድድር ለኦሎምፒክ ማጣሪያ በጥሩ ብቃትና ተክለ ቁመና አንደኛ ሆኖ ያለፈው የአዲስ አበባው አብዱልመሊክ በዋና ፌዴሬሽኑ እና በኦሎምፒክ ኮሚቴው አማካኝነት ያለምንም ምክንያት በሪዮ ኦሎምፒክ እንዳይሳተፍ ሲደረግ፤ በምትኩ ብቃትና ቅርፅ አልባው ሮቤል ኪሮስ፤ በአባቱና በኦሎምፒክ ኮሜቴው አማካኝነት እንዲሄድ መደረጉ እጅግ አሳዛኝና አሳፋሪ ክስተት ሆኖ ተመዝግቧል፡፡

ወደ ኦሎምፒኩ ውድድር መሄድ ያለበት ተወዳዳሪ እንዲቀር ከመደረጉ በተጨማሪ የውሃ ዋና አሰልጣኙ ዋናተኞች እንዲያሰለጥኑ በሪዮ ኦሎምፒክም ዋናተኞች ይዘው በዛውም ልምድ ቀስመው ለቀጣይ ዓለም አቀፍ በቃት ያላቸው ተወዳዳሪዎችን ማፍራት እንዲችሉ በሚል አሰልጣን አበበ ቢቂላ በማስታወቂያ በተደረገ ውድድ አልፈው ከሚሰሩበት ጋምቤላ ተጠርተው፣ የሪዮ ኦሎምፒክ ግብዣ ቢመጣላቸውም፤ የውሃ ዋና ፌሬሽን ፕሬዘዳንት በሆኑት የሮቤል አባት አቶ ኪሮስ ሃብቴ እና በኦሎምፒክ ኮሚቴው ፕሬዘዳንት አቶ ብርሃነ ኪዳነ ማርያም አማካኝነት አዲስ አበባ እንዲቀሩ ተደርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ያለ ብቃት ኦሎምፒክ ላይ እንዲሳተፍ የተደረገው ሮቤል ኪሮስ አሰልጣን አበበ ቢቂላ የኦሎምፒክ ጉዞውን እንዲሰርዝና አዲስ አበባ እንዲቀር የ10 ሺህ ብር ቼክ ጉቦ መስጠቱን፣ አሰልጣኙም ጉዳዩን ለዋና ፌሬሽን፣ ለኦሎምፒክ ኮሜቴ፣ ለስፖርት ኮሚሽን እና ለወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር ድረስ ቢያሳውቁም ምላሽ ሳያገኙ መቅረታቸው ሌላ ጥያቄን የሚያስነሳ ጉዳይ ነው፡፡

በውድድሩ በሮቤ፣ በአባቱ አቶ ኪሮስና በኦሎምፒክ ፖለቲካው ና ስጋዊ ዝምድና ምክንያት ሀፍረት ውስጥ የወደቀችው ሀገር፤ በአልማዝ አያና የሴቶች 10 ሺህ ሜትር ውድድር በአዲስ ክብረወሰን አንደኛ ሆና የወርቅ ሜዳሊያ ማምጣቷ ብዙዎችን አስደስቷል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን አትሌቷ በ5 ሺህ ሜትርም ተወዳድሯ ለሀገሯ የነሐስ ሜዳሊያንም በማምጣት ከማስደሰቷ በተጨማሪ ሁለት ወርቅ ባለማምጣቴ ህዝቡን ይቅርታ እጠይቃለሁ ያለችው ንግግር ይበልጥ የብዙዎችን ልብ ሰብሯል፡፡

አትሌት አልማዝ አያና ብቃት ብቻ ሳይሆን ትህትና እና ብሔራዊ ፍቅርን አንድ ላይ አንግባ በግሏ በአንድ የኦሎምፒክ ውድድር ብቻዋን ሁለት ሜዳሊያ ማምጣቷ ከኢትዮጵያውያን አልፎ ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብም ከፍተኛ አድናቆትና ክብርንም አጎናፅፏታል፡፡ በርግጥ በአንድ ኦሎምፒክ ሁለት ሜዳሊያ ስታመጣ ለኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ ባትሆንም፤የሪዮ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያውያን በብዙ የሀዘን እና የመከፋት እንዲሁም በውጤት ላይ ስጋት ውስጥ በነበሩበት ወቅት መሆኑ ልዩ ያደርገዋል፡፡

ሌላው በኢትዮጵያዊው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ አማካኝነት ከስፖርቱ በተጨማሪ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃንን ትኩረት የሳበነ፣ የተከፉና የተገፉ ኢትዮጵያውያንን በሁለት ነገሮች ያስደሰተ፤ ግን ደግሞ ለኢትዮጵያ እንዲሁም ለአፍሪካ ታሪክ አዲስ የሆነ፤ በኦሎምፒክ ታሪክ ደግሞ ሁለተኛ የሆነ አሳዛኝ ክስተት በሪዮ ኦሎምፒክ አደባባይ ታይቷል፡፡ አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ የኦሎምፒኩ መዝጊያ በሆነው በወንዶች ማራቶን ውድድር ሁለተኛ ሆኖ በማሸነፍ ለሀገሩ የብር ሜዳሊያ ቢያስገኝም፤ በሀገር ቤት መንግሥት በዜጎች ላይ እያደረሰ ያለውን ግድያ፣ እስር፣ ስቃይና እንግልት በመቃወም ለዓለም አደባባይ አሳይቷል፡፡ ተበድለናል የሚለውን ገላጭ ምልክቱን በፕሬስ መግለጫ እና በሽልማት ስነ ስርዓቱም ላይ ደግሞታል፡፡

የአትሌት ፈይሳ ያልተጠበቀው የተቃውሞ ክስተት ገዥውን ስርዓት ሀፍረት ውስጥ ቢከተውም፣ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውንን በተለይም በገዥው ስርዓት ግፍና በደል የተፈፀመባቸውን እንዲሁም ለዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብት የቆሙትን በሙሉ አስደስቷል፡፡ በመጨረሻም አትሌቱ ውድድሩን ሁለተኛ ሆኖ በሚያጠናቅቅበት ወቅት እጁን በመስቀለኛ አጣምሮ በተለይም ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ተቃውሞ በኋላም የኦሮሞ ተቃውሞ አሁን ደግሞ በአማራ ተቃውሞም ታስረናል፣ ተጨቁነናል፣ ተበድለናል፣ ነፃነት እንፈልጋለን የሚል መልዕክት ያለውን ምልክት እያሳየ ውድድሩ ሲያሸንፍ ታይቷል፡፡ ድርጊቱ ባለስልጣናቱን እና የስርዓቱን ደጋፊዎች እጅግ አስደንግጧል፡፡

አትሌት ፈይሳም በኦሎምፒኩ መድረክ የተገኙ የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ለምን ያንን ምልክት እንደተጠቀመ ሲጠየቅ፤ ሀገር ቤት በተለይ መንግሥት በኦሮሚያ በርካቶችን እየገደለ፣ እያሰረ ያለውን ድርጊት መቃወሙን ለመግለፅ እንደሆነ፣ ያቀረበውን ተቃውሞ ተከትሎ ሀገር ቤት ቢመለስ መንግሥት እንደሚገድለው፣ ምናልባት ባይገድለው እንኳ እንደሚያስረው አሊያም ከሀገር እንዳይወጣ ሊያደርገው እንደሚችል ስለሚሰጋ ወደ ሀገር ቤት እንደማይመለስ በማስታወቅ ለጊዜው ብራዚል ቀርቷል፡፡ ሌሎች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች እና የልዑካን ቡድን አባላቱ ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸው ታውቋል፡፡

በውጭ የሚገኙ የተለያዩ የኢትዮጵያውያን መገናኛ ብዙኃንም ቃለመጠይቅ ያደረጉለት ሲሆን፤ አትሌቱም የቅርብ ጓደኞቹና አብረውት የተማሩ ሳይቀሩ በባሌ፣ በአርሲ፣ እንዲሁም በተለያየ የኦሮሚያና አማራ ክልል ሰዎች እየተገደሉ እና እየታሰሩ መሆኑን በመግለፅ፤ ድርጊቱንም በመቃወም ምልክቱን እንዳሳየና ህዝቡም በአንድነት ተባብሮ ስርዓቱን ማስወገድ እንዳለበት እምነቱን ሲገልፅ ተሰምቷል፡፡ በተለይም ህዝቡ በዘር ከመከፋፈል ይልቅ ሁሉም ተባብሮ ስርዓቱን ማስወገድ እንዳለበት በአፅንዖት ሲናገር ተሰምቷል፡፡

በተለይ የመንግሥት ባለስልጣናት እና ደጋፊዎች የአትሌት ፈይሳ የኦሎምፒክ ማራቶን ድል የብር ሜዳሊያ እንዲሰረዝ የዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ላይ ጫና ለማድረግ ቢሞክሩም፤ ዓለም አቀፉ የኦሎምፒክ በበኩሉ የአትሌቱን ሜዳሊያ ሊነጥቅም ሆነ ምንም ዓይነት ርምጃ እንደማይወስድ ይፋ አድርጓል፡፡ በመጨረሻም የኢትዮጵያ መንግሥት አትሌቱ ወደ ሀገሩ መመለስ እንደሚችል እና ላሳየው ተቃውሞ ምምልክት በማሳየቱ ምንም እንደማይደርስበት ቢያሳውቅም፤ አትሌቱ ግን ወደ ሀገር ቤት መመለስ ለደህንነቱ አደጋ እንዳለው በመግለፅ ለጊዜ ብራዚል ሪዮ ዲ ጄኔሪዮ መቅረቱ ተረጋግጧል፡፡

በ2016ቱ የሪዮ ኦሎምፒክ የኢትዮጵያ ውጤት:

ውጤት የተወዳዳሪ ስም        የውድድር ዓይነት እና ርቀት      የተገኘው ሜዳሊያ
1ኛ. አልማዝ አያና                 በሴቶች 10,000 ሜትር           ወርቅ
2ኛ. ገንዘቤ ዲባባ                  በሴቶች 1,500 ሜትር               ብር
2ኛ. ፈይሳ ሌሊሳ                    በወንዶች ማራቶን                     ብር
3ኛ. ጥሩነሽ ዲባባ                   በሴቶች 10,000 ሜትር           ነሐስ
3ኛ. ታምራት ቶላ                   በወንዶች 10,000 ሜትር          ነሐስ
3ኛ. ማሬ ዲባባ                      በሴቶች ማራቶን                       ነሐስ
3ኛ. አልማዝ አያና                  በሴቶች 5,000 ሜትር               ነሐስ
3ኛ. ሐጎስ ገብረህይወት            በወንዶች 5,000 ሜትር            ነሐስ
አጠቃላይ ድምር                     8    ሜዳሊያ

በተለይ በኦሎምፒክ ውድድር ዘርፍ ኢትዮጵያ ካሏት በርካታ የወድድር መስክ ዕድሎች ውስጥ አብዛኛውን ለምን መጠቀም እንደማትፈልግ እስካሁን ግልፅ ባይሆንም፤ በውጤትም ሆነ በውድድር ዘርፍ እንዲሁም ውጤት ማነስ ብዙ ጥያቄ የሚያስነሱ ጉዳዮች አሉ፡፡ ይሁን እንጂ ስፖርቱ አጠቃላይ በፖለቲካ መዋቅር የተሳሰረ በመሆኑ እና በብቃት ሳይሆን በፖለቲካ ሹመት ከየክልሉ በሚመጡ ሹመኞች እና ለፖለቲካ ስርዓቱ ታማኝ የተባሉ ብቻ ከፌዴሬሽን፣ ኦሎምፒክ ኮሜቴ እና ስፖርት ኮሚሽን ስለሚሞሉ ስርዓቱ እስካለ ስፖርቱ ላይ የተለየ አዎንታዊ ለውጥ ሊመጣ እንደማይችል እሙን ነው፡፡ ምክንያቱም ከወረዳ እስከ ፌደራል ድረስ ባሉ የስፖርት ፌዴሬሽን እና ስፖርት ኮሚሽን የሚመለከታቸው ሰዎች ባላቸው የትምህርት ዝግጅት፣ ዕውቀት፣ ብቃት፣ ልምድና ተነሳሽነት ኃላፊነት የሚቀመጡ ሳይሆን ባላቸው የፖለቲካ ወገንተኝነት ብቻ የሚሾሙ አንዳንዶቹ ስለ ስፖርት ስራና አስፈላጊነት ምን እንደሆነ እንኳ የማያውቁ የፖለቲካ ሹመኞች የኃላፊነት ቦታውን ይዘው እንዳሉ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡

ብቃቱ ያላቸው የስፖርት አመራር ባለሙያዎች ብቻ ሳይሆን ተወዳዳሪዎችም ነፃ የወድድር ተሳትፎ ሊያገኙ የሚችሉባቸው ዕድሎችም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየመነመኑ መጥተዋል፡፡ ስለዚህ ሀገሪቱ ኦሎምፒክን ጨምሮ በሁሉም የስፖርት ዘርፎች ውጤታማ እንድትሆን በአጠቃላይ የስርዓት ለውጥ ካልመጣ አሁን ባለው አሰራር የሚሾሙ ሰዎች ቢቀያየሩ እንኳ የተለየ ውጤት መጠበቅ አስቸጋሪ ነው፡፡

በ2016ቱ የሪዮ ኦሎምፒክ አጠቃላይ ውጤት አሜሪካ 121 ሚዳሊያ (46 ወርቅ፣ 37 ብር እና 38 ነሐስ)፣ እንግሊዝ 67 ሜዳሊያ (27 ወርቅ፣ 23 ብር እና 17 ነሐስ)፣ ቻይና 70 ሜዳሊያ (26 ወርቅ፣ 18 ብር፣ 26 ነሐስ)፣ ራሽያ 56 ሜዳሊያ (19 ወርቅ፣ 18 ብር እና 19 ነሐስ) እንዲሁም ጀርመን 42 ሜዳሊያ (17 ወርቅ፣ 10 ብር እና 15 ነሐስ) በማግኘት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከ1ኛ እስከ 5ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ አጠናቀዋል፡፡

የበጋው የሪዮ ኦሎምፒክ 207 የዓለም ሀገሮች የተውጣጡ 11,303 ተወዳዳሪዎች የተሳተፉበት ዓለም አቀፍ ዝግጅት ባለፈው እሁድ ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በመዝጊያው የማራቶን ውድድር በሰላም ተጠናቋል፡፡ በቀጣይም በ2018 የክረምት ኦሎምፒክ በደቡብ ኮሪያዋ ፓዮንቻን የሚካሄድ ሲሆን፤ የ2020ው የበጋው ኦሎምፒክ ውድድር ደግሞ በጃፓኗ መዲና ቶክዮ እንደሚዘጋጅ ይጠበቃል፡፡

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: