ዛሬ እሁድ መስከረም 22 ቀን 2009 ዓ.ም. ከአዲስ አበባ ደቡብ ምስራቅ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ደብረዘይት/ቢሾፍቱ ከተማ በሚገኘው ሆራ ሐይቅ አካባቢ በኦሮሞ ማኀበረሰብ እና በሌሎች ኢትዮጵያውያን እንደቀደሙ ዓመታት ሁሉ ጊዜውን ጠብቆ ዛሬ እየተከበረ ባለው የኢሬቻ ክብረ በዓል ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ድረስ በግማሽ ቀን ብቻ ከ250 በላይ የበዓሉ ታዳሚ ሰላማዊ ዜጎች በገዥው ስርዓት በተወሰደ ወታደራዊ የኃይል ርምጃ መገደላቸው ተጠቆመ፡፡

በስፍራው ተገኝተው የነበሩ የዓይን እማኞች እና የሆስፒታል ምንጮች ከሆነ ከአንድ ሺህ ያላነሱ ንፁሃን ዜጎችም ቆስለው በደብረዘይት እና አዲስ አበባ በሚገኙ ሆስፒታሎች ለህክምና እርዳታ መላካቸው ታውቋል፡፡
ዛሬ ሰላማዊ ዜጎች ላይ በአንድ ቀን ብቻ በመንግሥት የተፈፀመው ግድያ ከህዳር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ከ650 በላይ፣ በአማራ ከሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ከ200 በላይ ከተገደሉ ንፁሃን በተጨማሪ የተፈፀመ ዘግናኝ ግድያ ነው፡፡ በተለይ በበዓሉ ስፍራ የነበሩ የዓይን እማኞች ከሆነ የተገደሉ ዜጎች ቁጥር ከተጠቀሰው በላይ ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል፡፡ በዘንደሮው በዓል ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢ የመጡ የበዓሉ ታዳሚዎች ቁጥር እስከ 2 ሚሊዮን እንደሚደርስ ተገምቷል፡፡
መንግሥት በሚቆጣጠራቸው መገናኛ ብዙኃን እና በቃል አቀባይ ጽህፈት ቤቱ በኩል በሰጠው መግለጫ ሟቾቹ በተፈጠረ ግርግር እንደሆነ ቢያሳውቅም፤ የዓይን እማኞች በበኩላቸው በበዓሉ ላይ ወጣቶች እጃቸውን በማጣመር ከዚህ ላለፉት 10 ወራት መንግሥት በዜጎች ላይ የፈፀመውን ግድያ እና እስር የሚያወግዝ ተቃውሞ እያቀረቡ ባሉበት ሰዓት በገዥው ስርዓት ወታደሮች አስለቃሽ ጢስን እና ተከታታይ ተኩስ በህዝቡ ላይ እንደተከፈተ ተናግረዋል፡፡ በጥይት ከተገደሉት በተጨማሪ ከተኩሱ ለማምለጥ የሞከሩ ሰዎችም በጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ገብተው የሞቱ፣ የተገዱና የተረፉም እንዳሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡
መንግሥት ለንፁሃን መሞት ምክንያቱ አመፅ ቀስቃሾ በፈጠሩት ግርግር በመረጋገጣቸውና ገደል ውስጥ በመግባታቸው ነው ቢልም፤ የበዓሉ ታዳሚዎች በበኩላቸው የበዓሉን ድባብ በማጥፋ ወታደሮች የበዓሉ ታዳሚ ሰላማዊ ዜጎች ላይ ተኩስ በመክፈት ግድያው ሆን ተብሎ የተፈፀሙውና ንፁሃን እንዲሞቱ የተደረገው በገዥው ስርዓት እንደሆነ ከጉዳቱ የተረፉ እማኞች ተናግረዋል፡፡
የኦሮሞ ማኀበረሰብ መብት አራማጆችን ጨምሮ ሌሎች ኢዮጵያውያን የመብት አራማጆች የተገደሉ በርካታ ዜጎችን ምስልና ቪዲዮ በማኀበራዊ ሚዲያ ሲያሰራጩ ተስተውሏል፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ በህዝብ ክብረ በዓል ላይ የዛሬውን ያህል ዜጎች በመንግሥት ወታደራዊ ኃይሎች ሰላማዊ ዜጎች ላይ በወሰዱት ርምጃ ሲገደሉ የመጀመሪያው ነውም ተብሏል፡፡
የኢሬቻ በዓል በኦሮሞ ማኀበረሰብ ዘንድ ጥንታዊ የሆነ ፈጣሪን በጋራ የማመስገን በዓል ሲሆን፤ ከኦሮሞ ማኀበረሰብ በተጨማሪ ከተለያዩ አካባቢዎች ሌሎች ኢትዮጵያውያን በብዛት የሚታደሙበትና የሚያከብሩት ታላቅ ህዝባዊ በዓል መሆኑ ይታወቃል፡፡
በተያያዘ ዜና፤ የኤሬቻ በዓል ጅምላ ግድያን ተከትሎ በአምቦ እና አወዳይ ከተማ ህዝባዊ ተቃውሞ የተቀሰቀሰ ሲሆን፤ በሁለቱም ከተሞች መንግሥት ወታደሮች የኃይል ርምጃ መውሰድ መጀመራቸው ተገለፀ፡፡ በተወሰደው ርምጃ ምን ያህል ዜጎች ጉዳት እንደደረሰባቸው ለጊዜው ማወቅ አልተቻለም፡፡