በኢትዮጵያ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታወጀ፤ ህዝባዊ ተቃውሞውም አድማሱን እያሰፋ ቀጥሏል

(አዲስ ሚዲያ)በኢትዮጵያ ለተከታታይ አስር ወራት የፈጀው የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከትናንት ቅዳሜ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለ6 ወር ተግባራዊ የሆነ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማውጣቱን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ መስከረም 29 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ዝርዝር ጉዳይን በተመለከተ ወደፊት ይገለፃል ከማለት በስተቀር አጠቃላይ ይዘቱን በተመለከተ ያሉት ነገር የለም፡፡

በሌላ በኩል በጠቅላይ ሚኒስተሩ በሚመራ ኮማንድ ፖስት ስር የህግ አስከባሪዎችም መከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ፣ የፌደራል የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል፣ የአካባ ሚሊሻዎች እና ንብረት ጠባቂ የፀጥታ ኃይሎች የሚያካትት መሆኑን ደግሞ ጠቅላይ አቃቤ ህጉ አቶ ጌታቸው አምባዬ አብራርተዋል፡፡ አስቸኳይ አዋጁ በአጠቃላይ ሀገሪቱ ላይ ተግባራዊ መደረጉንም ጠቅላይ አቃቤ ህጉ አስታውቀዋል፡፡

halemariam-desalegn

ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አተገባበር መሰረት የተጠረጠረ ማንኛቸውም ሰው ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሊታሰር እንደሚችል፣ ቤቶችና አካባቢዎችም ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ብርበራ ሊካሄድባቸው እንደሚችልም እና ማንኛውም ዓይነት መገናኛ ብዙኃን ሊዘጋ እንደሚችልም ጠቅላይ አቃቤ ህጉ ይፋ አድርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ተቃውሞን ሊገልፁ የሚችሉ ምልክቶችን መጠቀምንም አዋጁ እንደሚከለክል፣ አዋጁን ተላልፎ የተገኘም ቅጣት እንደሚጠብቀው አስታውቀዋል፡፡

በተለይ ከህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ እንዲሁም ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በአማራ ክልል የተነሱ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞች መንግሥት በወታደራዊ ኃይል ግድና፣ እስርና አፈና ለማስቆም መሞከሩን ተከትሎ ያለማቋረጥ ተቃውሞዎቹ ተጠናክረው መቀጠላቸው ስርዓቱን ስጋት ላይ ጥሎታል፡፡ በተለይ እንደ ማዕከላዊ ስታስቲክስ ኤጀንሲ መረጃ ከሆነ ከሀገሪቱን አጠቃላይ ህዝብና የቆዳ ስፋት 62% የሚሸፍነው የሀገሪቱ ህዝብ በአደባባይ የስርዓት ለውጥ እንደሚፈልግና በስልጣን ላይ ባለው ስርዓት መገዛት ለከፍተኛ ግድያ፣ እስር፣ በደልና ጭቆና እንደዳረገው በአደባባይ እየገለፀ ይገኛል፡፡ ለህዝቡ ጥያቄ የመንግሥት ምላሽ ግድያ፣ እስርና ማሰቃየት መሆኑ ደግሞ ህዝቡን የበለጠ እንዲቆጣና የተቃውሞ አድማሱን እንዲያሰፋ እንዳስገደደው ይነገራል፡፡

በተለይ ባለፈው እሁድ መስከረም 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሞ ማኀበረሰብ ዘንድ ትልቅ ስፍራ የሚሰጠውና በርካታ ኢትዮጵያውያን የሚታደሙበት የኢሬቻ በዓል በደብረዘይት/ቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ሐይቅ እየተከበረ ባለበት ወቅት ህዝቡ በሰላማዊ መንገድ አገዛዙ ላይ ተቃውሞውን ማሰማቱን ተከትሎ በተወሰደው ርምጃ አጠቃላይ ከ678 በላይ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው በመላው ኢትዮጵያ የበለጠ ቅሬታን ፈጥሯል፡፡ በዚህም በኦሮሚያ ክልል የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደ ህዝባዊ አብዮት መሸጋገሩንም የኦሮሞ መብት አራማጆች ይፋ ማድረጋቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ የአገዛዙ ሰዎች፣ ደጋፊዎችና ተባባሪዎች ናቸው የተባሉ ንበረቶች እና አገዛዙ የሚጠቀምባቸው የተለያዩ መንግሥታዊ ተቋማት ላይ ርምጃ መውሰዳቸው ታውቋል፡፡ የኦሮሞ ህዝባዊ ተቃውሞ አሁንም ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፤ የመንግሥት ወታደራዊ የኃይል ርምጃም ተጠናክሮ በመቀጠል የበርካታ ሰላማዊ ዜጎች ህይወት ጠፍቷል፡፡

በተመሳሳይ በአማራ ክልል ባለው ህዝባዊ ተጋድሎ የቀጠለ ሲሆን፤ የመንግሥት ወታደራዊ እርምጃ በርካታ ሰላማዊ ዜጎችን ህይወት ቀጥፏል፡፡ በኦሮሚያ እና አማራ ክልል በተጨማሪ በደቡብ ክልል ኮንሶ ወረዳም ተመሳሳይ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ እና የመንግሥት የኃይል ርምጃ የቀጠለ ሲሆን፤ በዚህም በርካታ ሰላማዊ ዜጎች ተገድለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በዛው ደቡብ ክልል ጌዲዮ ዞን ባሉ ወረዳዎችና ከተሞች ከፍተኛ ተቃውሞና ግጭቶች ተቀስቅሰዋል፡፡ በዚህም የሰው ህይወት መጥፋትን ጨምሮ የበርካታ ሰላማዊ ዜጎች የንግድ ሱቆችና መኖሪያ ቤቶች ተቃጥለዋል፡፡ የተለያዩ የኃይማኖት ተቋማትም ላይ ጥቃት መሰንዘሩን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ አጠቃላይ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል እንዲሁም በደቡብ ክልል ኮንሶ ወረዳ ባሉ ህዝባዊ ተቃውሞዎች በመንግሥት ወታደራዊ የኃይል ርምጃ የተገደሉ ሰላማዊ ዜጎች ቁጥር ከ 1,420 በላይ መድረሳቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ መንግሥት በበኩሉ ህዝባዊ ተቃውሞቹ በውጭ ኃይል የተቀነባበሩ ናቸው በማለት ለመሸፋፈን ቢሞክርም ከህዝቡ፣ ከመብት አራማጆችም ሆነ ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ተቀባይነት አላገኘም፡፡

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: