ዮናስ ዓብይ እና ውድነህ ዘነበ
ባለፈው ሳምንት ዓርብ መስከረም 27 ቀን 2009 ዓ.ም. በደቡብ ክልል ጌዲዮ ዞን የተቀሰቀሰው ደም አፍሳሽ ግጭት፣ ለበርካታ ሰዎች ሕይወት መጥፋትና ንብረት ውድመት ምክንያት ሆነ፡፡
ከጌድዮ ዞን እየወጡ ያሉ መረጃዎች ባለፈው ዓርብ ከቀኑ 4፡30 ሰዓት ተጀምሮ እስከ ቅዳሜ ድረስ በቀጠለው ደም አፍሳሽ ግጭት የ63 ሰዎች ሕይወት ማለፉን ይጠቁማሉ፡፡ ከጌዲዮ ብሔረሰብ አባላት 52 ሰዎች፣ ከሌሎች ክልሎች መጥተው በዲላ ከተማ ከሚኖሩ ውስጥ ደግሞ 11 የሚደርሱ ግለሰቦች ሕይወት ማለፉን ምንጮች ተናግረዋል፡፡ በዚህ ግጭት መኖሪያ ቤቶች፣ የንግድ ተቋማት፣ የሕዝብና የጭነት ተሽከርካሪዎችና የቤት መኪኖች በእሳት ጋይተዋል፡፡ የክልሉ መንግሥት ግን ቁጥሩ የተጋነነ ነው ይላል፡፡
የደቡብ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አህመድላዲን ጀማል በተቀሰቀሰው ግጭት የሰው ሕይወት ማለፉንና ንብረት መውደሙን ለሪፖርተር አረጋግጠዋል፡፡
ነገር ግን ምክትል ኮሚሽነሩ እንደገለጹት፣ የሟቾችን ቁጥርና የደረሰውን የንብረት ውድመት የሚያጣራ ግብረ ኃይል ወደ ሥፍራው በመላኩና ሪፖርቱን ባለማጠናቀቁ፣ የሟቾችንም ሆነ የደረሰውን የንብረት ውድመት በቁጥር ማስደገፍ አይቻልም፡፡
መስከረም 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ከረፋዱ 4፡30 ሰዓት ላይ የጌዲዮ ተወላጅ የሆኑ ሰዎች በተለይ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍል የመጡ የዲላ ከተማ ነዋሪዎች ላይ መጠነ ሰፊ ጥፋት መፈጸማቸውን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ምንጮች እንደገለጹት የጥቃቱ ማጠንጠኛ ከሌሎች አካባቢዎች የመጡ ሰዎች በዞኑ ውስጥ ሀብትና ንብረት ማፍራታቸው፣ በአንፃሩ ደግሞ የጌዲዮ ብሔረሰብ አባላት በድህነት ውስጥ ነን በሚል ምክንያት ለዓመታት በአካባቢው የሚኖሩ የሌሎች ክልል ተወላጆች ከአገር እንደሚወጡ መጠየቃቸው ነው፡፡
በዚህ ሳቢያ የከተማው ነዋሪዎች ቤቶቻቸውና ንብረቶቻቸው ከመውደማቸውም በተጨማሪ ግድያ ተፈጽሞባቸዋል፡፡ ከከተማ እንዲወጡ የተደረጉም አሉ፡፡
ለዚህ ግጭት መነሻ የሆነው በዲላ ከተማ ‘ታይዋን’ ተብሎ በሚጠራው የገበያ ሥፍራ አካባቢ በጌዲዮ የገበሬዎች ኅብረት ሥራ ዩኒየንና በከተማው ነጋዴዎች መካከል የመሬት ይገባኛል ጥያቄ በፍርድ ቤት እልባት ማግኘቱ ነው፡፡
በሁለቱ አካላት መካከል ሲካሄድ የቆየው የፍርድ ቤት ክርክር ለከተማው ነጋዴዎች መወሰኑ ቁጣ ቀስቅሷል፡፡ በውሳኔው የተነሳም የአካባቢው ነዋሪዎች ቁጣ ወደ ደም አፍሳሽ ግጭት ተቀይሯል፡፡
የእዚህ ግጭት ሰለባ የሆኑ የዲላ ከተማ ነጋዴ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በከተማ ከሚኖሩ ሌሎች ብሔሮች አባላት መካከል 11 የሚሆኑ ሞተዋል፡፡ እንዲሁም ከጌዲዮ ወገኖች 52 ያህል መገደላቸውን አስረድተዋል፡፡
የደቡብ ክልል የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሂክማ ኬይረዲን ለሪፖርተር እንገደለጹት ግን አጠቃላይ የሟቾች ቁጥር 23 ሲሆን፣ ግጭቱም ብሔር ተኮር አይደለም፡፡
በዚህ ግጭት የዲላ ከተማን ሲሶ ያህሉን እሳት በልቶታል፡፡ ‹‹ፌዴራል ፖሊስ ቅዳሜ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ባይደርስ ሁላችንም እናልቅ ነበር፤›› በማለት የግጭቱን አስከፊነት ነጋዴው ገልጸዋል፡፡
የጌዲዮ ዞን መቀመጫ የሆነችው ዲላ ከአዲስ አበባ ከተማ 369 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡ ዞኑ በአጠቃላይ 1,347.04 ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት አለው፡፡
ዞኑ የኢትዮጵያ ስፔሻሊቲ ቡና (ይርጋ ጨፌ) ይመረትበታል፡፡ በዞኑ ዲላ፣ ጨለልቅቱ፣ ይርጋ ጨፌና ወናጎ አጎራባች አካባቢዎች ግጭቱ ተንሰራፍቶ ነበር፡፡
የፖሊስ ምክትል ኮሚሽነሩ እንዳሉት፣ በአሁኑ ወቅት የክልሉ ሰላም ወደነበረበት ተመልሷል፡፡ ችግሩንም የፈጠሩ አካላትም በቁጥጥር ሥር እየዋሉ ነው፡፡ እስከ ማክሰኞ ጥቅምት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ሰላም ቢሰፍንም በከተማው የንግድ እንቅስቃሴ አለመጀመሩ ታውቋል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ