(አዲስ ሚዲያ) የፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ እና መስራች የነበረው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ባለፈው ህዳር 2007 ዓ.ም. በመንግሥት በተመሰረተበት ክስ የ3 ዓመት ፅኑ እስር ተፈርዶበት ዝዋይ ወህኒ ቤት የነበረ ቢሆንም፤ ከፋለፈው ማክሰኞ ህዳር 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ የነበረበት ዘዋይ ወህኒ ቤትን ጨምሮ ቃሊቲ፣ የአቃቂ ቂሊንጦ እና ሸዋ ሮቢት ወህኒ ቤት ጥበቃ ሰራተኞችና ኃላፊዎች፤ ጋዜጠኛ ተመስገን የት እንዳለ ከቤተሰቦቹ ለቀረበላቸው ጥያቄ በተጠቀሱት ወህኒ ቤቶች እንደሌለ በመግለፅ በአሁን ወቅት የት እንዳለ ግን እንደማያውቁ መናገራቸውን የጋዜጠኛው ቤተሰቦች ይፋ አድርገዋል፡፡
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፤ ፎቶ ከማኀበራዊ ገፅ
አዛውንቱ ወላጅ እናቱን ጨምሮ ሌሎች የጋዤተኛው ቤተሰቦችና ወዳጆች ቀደም ሲል ታስሮ የነበረበትን እና በፌደራል ደረጃ የሚታወቁ ወህኒ ቤቶች በሙሉ በመሄድ ያለበትን ሁኔታ ለማረጋገጥ ሙከራ ቢያደርጉም ሊያገኙት እንዳልቻሉ የተገለፀ ሲሆን፤ በተለይ በዕድሜ የገፉ አዛውንት ወላጅ እናቱ ወ/ሮ ፋንታዬ እርዳቸው በከፍተኛ ስጋትና ጭንቀት ላይ መሆናቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ ጋዜጠኛው ቀደም ሲል በእስር ላይ እያለ በደረሰበት ህመም ምክንያት የህክምና ዕርዳታ ለማግኘት ጠይቆ በተደጋጋሚ መከልከሉ አይዘነጋም፡፡
የፌደራል አቃቤ ህግ ጋዜጠኛ ተመስገን በፍትህ ጋዜጣ ላይ በፃፋቸው ፅሑፎችን ዋቢ በማድረግ በመሰረተበት ክስ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት 3 ዓመት ፅኑ እስራት እና የፍትህ ጋዜጣ አሳታሚ ማስተዋል ህትመትና ማስታወቂያ ድርጅትደግሞ 10 ሺህ ብር እንዲቀጣ መበየኑ ይታወሳል፡፡ጋዜጠኛ ተመስገን ከመታሰሩ በፊት መንግሥት ይፈፅማል ያላቸው የመብት ረገጣዎችና ብልሹ አሰራሮችን በግልፅ በመተቸት ይታወቃል፡፡
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን ጨምሮ በገዥው የኢህአዴግ መንግሥት 11 ጋዜጠኞችና 1 ብሎገር ኢትዮጵያውያን እንዲሁም 3 የውጭ ዜጋ ጋዜጠኖች በአጠቃላይ 15 ጋዜጠኞችና ብሎገር በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይ በእስር ከሚገኙ ጋዜጠኞች መካከል ኢትዮጵያውያኑ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ ውብሸት ታዬ፣ ተመስገን ደሳለኝ፣ ጌታቸው ሽፈራው፣ ፈቃዱ ምርከና፣ጌታቸው ወርቁ፣ አናኒያ ሶሪ፣ ኤልያስ ገብሩ፣ በፈቃዱ ኃይሉ፣ ከድር መሐመድ፣ ዳርሰማ ሶሪ እና የደ ብርሃን ብሎገር ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ተጠቃሾች ናቸው፡፡
እንደ ሀገር ውስጥ የሰብዓዊና የፕሬስ ነፃነት መብት ተሟጋቾች እና እንደ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መረጃ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ በአሁን ወቅት የፕሬስ ነፃናት ከሌለባቸው የዓለም ሀገራት ተርታ በቀዳሚነት ከሚጠቀሱት አንዷ ስትሆን፤ በርካታ ጋዜጠኞችን በማሰር በአፍሪካ ከጎረቤት ኤርትራ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ ሀገር ነች፡፡