በአማራ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ጎንድር ውስጥ ለእስር ተዳርጋ ወደ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ተዛውራ ከአራት ወራት በላይ ያሳለፈችው አክቲቪስት ንግስት ይርጋና ሌሎች አምስት ሰዎች የሽብር ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡
ንግስት ይርጋ
የፌደራል አቃቤ ህግ ታህሳስ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. በጻፈውና ለተከሳሾች ጥር 1 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲደርሳቸው በተደረገው የክስ ቻርጅ ላይ እንደተመለከተው ንግስት ይርጋ ‹‹ከአርበኞች ግንቦት ሰባት የሽብር ድርጅት ጋር ግንኙነት በመፍጠር፣ በሰሜን ጎንደርና በሌሎች የአማራ ክልል አካባቢዎች አመጽ በማስነሳት፣ አመጹን በበላይነት በመምራትና በማስቀጠል…›› የሽብር ወንጀል ድርጊት ተሳታፊ በመሆን ክስ ቀርቦባታል፡፡
ንግስት ይርጋ 1ኛ ተከሳሽ በተደረገችበት የክስ ዝርዝር ላይ እንደተመለከተው፣ ተከሳሾች በ2001 ዓ.ም የወጣውን የጸረ ሽብር አዋጅ አንቀጽ 3/4/6ን በመተላለፍ ተከሰዋል፡፡
የመብት አራማጅ ንግስት ይርጋ ነሐሴ ወር ላይ በጎንደር ከተማ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ‹‹የአማራ ህዝብ አሸባሪ አይደለም›› የሚል ጽሁፍ የሰፈረበት ቲሸርት ለብሳ በሰልፉ ላይ መታየቷ ይታወሳል፡፡
ክሱ የቀረበለት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበውን ክስ በንባብ ለማሰማት ለጥር 10 ቀን 2009 ዓ.ም ቀጠሮ ይዟል፡፡
ምንጭ፦ EHRP