ኢትዮጵያዊው የህዋና ስነፈለክ መምህር እና ተመራማሪ ዶክተር ለገሰ ወትሮ እርፉ። ዶ/ር ለገሰ ሚያዝያ 19 ቅን 2009 ዓ.ም. አዲስ አበባ በልጃቸው መኖሪያ ቤት ሳሉ በ67 ዓመታቸው በድንገት ህይወታችው አልፏል። መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከሆነ የሞታቸው ምክንያት ከዚህ ቀደም የነበረባቸው የልብ ድካም ህመም እንደሆነ ታውቋል። የቀብር ስነ ስርዓታቸውም በአዲስ አበባ ጳውሎስ ወጴጥሮስ ቤተክርስቲያን ተፈፅሟል።
ዶ/ር ለገሰ ወትሮ በቀድሞ አርሲ ክፍለ ሀገር አርሲ ነጌሌ ስሬ ከተማ የተወለዱ ሲሆን፥ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታችውንም በትውልድ ከተማችው በማጠናቀቅ፥ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታችውን ደግሞ በአሰላ እና በአዲስ አበባ በዕደማርያም ትምህርት ቤት እጠናቀዋል። በመቀጠልም ከአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በፊዚክስ የመጀመሪያ እና የሁለተኛ ድግሪያቸውን ያገኙ ሲሆን፥ በተጨማሪ ከእንግሊዙ ሼፊልድ ዩኒቨርስቲ በፊዚክስ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል።
የዶክተሬት ዴጌሪያቸውንም በፊዚክስ ስነ ፈለክና ህዋ ሳይንስ ትምህርት መስክ ከአሜሪካ ዩኒቨርስቲ ኦፍ ካሊፎርኒያ ያገኙ ሲሆን፥ ህይወታቸው እስካለፈ ድረስ በምድብኛ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር በመሆን ሲያገለግሉ የነበረ ሲሆን፥ በተጋባዥ መምህርነትም በተለያዩ የዓለም ሀገራትም ያስተምሩ እንደነበር ይታወቃል።
ዶ/ሩ ከመምህርነት በተጨማሪ በፊዚክስ የስነ ፈለክና ህዋ ሳይንስ ንድፈ ሀሳብ ሳይንቲስት ሲሆን በዘርፉ ለዓለም ባበረከቱት አስተዋፅዖ እ አ አ በ2011 በአሜሪካ በተደረገ ሽልማት “ምርጥ የዓመቱ ሰው” በሚልም የተሸለሙ ኢትዮጵያዊ አፍሪካዊ ምሁር ነበሩ። ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትዮጵያ ስነፈ ለክና ህዋ ሳይንስ ማኅበርን በመመስረትና መሪ በመሆን ከማገሌገላቸው በተጨማሪ የአፍሪካ ስነ ፈለክና ህዋ ሳይንስ ማኅበር መስራች አባል እንዲሁም የዓለም አቀፉ የስነ ፈልክና ህዋ ሳይንስ አባልና የአመራር ቦርድ አባል በመሆን ማገልገላቸው ታውቋል።
በተለይ በኢትዮጵያ የፊዚክስ ፥ ስነ ፈለክና ህዋ ሳይንስን ለመጀመሪያ ጊዜ በሬዲዮና በመፅሔቶች በማቅረብና በመተንተን በሰፊው ይታወቃሉ። የተለያዩ የጥናትና ምርምር ስራዎቻቸውንም በተለያዩ ዓለም አቀፍ የጥናት ማዕከላት በማሳተም ለዓለም እንዲዳረስ ማድረጋቸውም ይታወቃል።