በኢትዮጵያ 2010 አዲስ ዓመት ህዝባዊ ተቃውሞዎች ዳግም ተቀሰቀሰ። በተለይ በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ከተሞች በገዥው መንግሥት ላይ ዳግም ህዝባዊ ተቃውሞች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ተከትሎ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት ወታደራዊ የኃይል ርምጃ 8 ያህል ሰዎች መገደላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል።
ባለፈው ህዳር 2008 ዓ. ም. ጀምሮ ክዓመት በላይ የዘለቀው የኦሮሚያ፥ አማራ እና ደቡብ ክልል በተለይም ኮንሶ አካባቢ የተከሰተውን ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ ተከትሎ ሀገሪቱ ለ10 ወራት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር እንደነበረች ይታወሳል። ይሁን እንጂ በአስችኳይ አዋጁ ጊዜ ህዝባዊ አመፁ የተረጋጋ ቢመስልም በያዝነው ጥቅምት 2010 ዓ .ም. ዳግም ማገርሸቱ ታውቋል።
የህዝቡ ተቃውሞ ዋነኛ ምክንያት ተደርጎ የተጠቀሰውም ባለፈው መስከረም 2010 ዓ ም በኦሮሚያ እና በኦጋዴን የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ድንበር አካባቢ በተቀሰቀሰ ግጭት በርካታ ሰላማዊ ዜጎች መገደላችውን እና በኦጋዴን የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል አስተዳደርና በክልሉ ልዩ ኃይል ፖሊስ አማካኝነት ከ70,000 በላይ ዜጎች ከሚኖሩበት ቀዬ መፈናቀላቸውን በመቃወም እንዲሁም የታአሰሩ የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ የሚል ጥያቄም እንደነበር ለማወቅ ተችሏል።
በተለይ ባለፈው መስከረም 2010 ዓ ም በሁለቱ ክልሎች ድንበር አካባቢ በተቀሰቀሰ ግጭት ከሁለትም ክልል በርካታ ንፁሃን ዜጎች መገደላቸው ይታወሳል።
ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስም በተለይ በኦሮሚያ ክልል ባሉ አንዳንድ ከተሞች ህዝባዊ ተቃውሞች መቀጠላቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል።